አንደኛ ነገሥት 12:1-33

  • ሮብዓም ለሕዝቡ የሰጠው መጥፎ ምላሽ (1-15)

  • አሥሩ ነገዶች ዓመፁ (16-19)

  • ኢዮርብዓም የእስራኤል ንጉሥ ሆነ (20)

  • ሮብዓም ከእስራኤላውያን ጋር እንዳይዋጋ ተነገረው (21-24)

  • ኢዮርብዓም ያቋቋመው የጥጃ አምልኮ (25-33)

12  ሮብዓም እስራኤላውያን በሙሉ ሊያነግሡት+ ወደ ሴኬም+ መጥተው ስለነበር እሱም ወደ ሴኬም ሄደ።  የናባጥ ልጅ ኢዮርብዓም ይህን እንደሰማ (ምክንያቱም ኢዮርብዓም ከንጉሥ ሰለሞን ሸሽቶ በግብፅ ይኖር ስለነበር በወቅቱ በዚያ ይገኝ ነበር)፣+  ልከው አስጠሩት። ከዚያም ኢዮርብዓምና መላው የእስራኤል ጉባኤ መጥተው ሮብዓምን እንዲህ አሉት፦  “አባትህ ቀንበራችንን አክብዶብን ነበር።+ አንተ ግን አባትህ የሰጠንን አስቸጋሪ ሥራና በላያችን የጫነብንን ከባድ* ቀንበር የምታቀልልን ከሆነ እናገለግልሃለን።”  በዚህ ጊዜ “እንግዲያው ሂዱና ከሦስት ቀን በኋላ ተመልሳችሁ ኑ” አላቸው። በመሆኑም ሕዝቡ ሄደ።+  ከዚያም ንጉሥ ሮብዓም አባቱ ሰለሞን በሕይወት በነበረበት ጊዜ ሲያገለግሉት የነበሩትን ሽማግሌዎች “ለዚህ ሕዝብ ምን ምላሽ እንድሰጥ ትመክሩኛላችሁ?” በማለት ምክር ጠየቀ።  እነሱም “ዛሬ አንተ የዚህ ሕዝብ አገልጋይ ብትሆንና የጠየቁህን ብትፈጽምላቸው እንዲሁም መልካም ምላሽ ብትሰጣቸው ምንጊዜም አገልጋዮችህ ይሆናሉ” በማለት መለሱለት።  ሆኖም ሮብዓም ሽማግሌዎቹ የሰጡትን ምክር ትቶ አብሮ አደጎቹ ከነበሩትና አሁን የእሱ አገልጋዮች ከሆኑት ወጣቶች ጋር ተማከረ።+  እሱም እንዲህ ሲል ጠየቃቸው፦ “‘አባትህ የጫነብንን ቀንበር አቅልልልን’ ለሚለኝ ለዚህ ሕዝብ ምን ምላሽ እንድንሰጥ ትመክሩኛላችሁ?” 10  አብሮ አደጎቹ የሆኑት ወጣቶችም እንዲህ አሉት፦ “‘አባትህ ቀንበራችንን አክብዶብን ነበር፤ አንተ ግን ቀንበራችንን አቅልልልን’ ለሚልህ ለዚህ ሕዝብ እንዲህ በለው፦ ‘ትንሿ ጣቴ ከአባቴ ወገብ ትወፍራለች። 11  አባቴ ከባድ ቀንበር ጭኖባችሁ ነበር፤ እኔ ግን ቀንበራችሁን የባሰ አከብደዋለሁ። አባቴ በአለንጋ ገርፏችሁ ነበር፤ እኔ ግን በእሾህ አለንጋ እገርፋችኋለሁ።’” 12  ኢዮርብዓምና መላው ሕዝብ ንጉሡ “በሦስተኛው ቀን ተመልሳችሁ ኑ” ባላቸው መሠረት በሦስተኛው ቀን ወደ ሮብዓም መጡ።+ 13  ንጉሡ ግን ሽማግሌዎቹ የሰጡትን ምክር ትቶ ለሕዝቡ መጥፎ ምላሽ ሰጠ። 14  ወጣቶቹም በሰጡት ምክር መሠረት “አባቴ ቀንበራችሁን አክብዶባችሁ ነበር፤ እኔ ግን ቀንበራችሁን የባሰ አከብደዋለሁ። አባቴ በአለንጋ ገርፏችሁ ነበር፤ እኔ ግን በእሾህ አለንጋ እገርፋችኋለሁ” አላቸው። 15  በመሆኑም ንጉሡ ሕዝቡን ሳይሰማ ቀረ፤ ይህም የሆነው ይሖዋ በሴሎናዊው በአኪያህ+ አማካኝነት ለናባጥ ልጅ ለኢዮርብዓም የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ ይሖዋ እነዚህ ነገሮች በዚህ መንገድ እንዲከናወኑ ስላደረገ ነው።+ 16  እስራኤላውያን ሁሉ ንጉሡ ሊሰማቸው ፈቃደኛ አለመሆኑን ሲያዩ ንጉሡን እንዲህ አሉት፦ “ከዳዊት ምን ድርሻ አለን? ከእሴይ ልጅ ምንም ርስት የለንም። እስራኤል ሆይ፣ ወደ አማልክትህ ተመለስ። ዳዊት ሆይ፣ እንግዲህ የገዛ ቤትህን ጠብቅ!” ከዚያም እስራኤላውያን ወደየቤታቸው* ተመለሱ።+ 17  ይሁንና ሮብዓም በይሁዳ ከተሞች በሚኖሩት እስራኤላውያን ላይ መግዛቱን ቀጠለ።+ 18  ከዚያም ንጉሥ ሮብዓም የግዳጅ ሥራ እንዲሠሩ የተመለመሉት ሰዎች አለቃ የነበረውን አዶራምን+ ላከው፤ ሆኖም እስራኤላውያን በሙሉ በድንጋይ ወግረው ገደሉት። ንጉሥ ሮብዓም ግን እንደ ምንም ብሎ ሠረገላው ላይ በመውጣት ወደ ኢየሩሳሌም ሸሸ።+ 19  እስራኤላውያንም እስከዚህ ቀን ድረስ በዳዊት ቤት ላይ እንዳመፁ+ ናቸው። 20  እስራኤላውያን በሙሉ ኢዮርብዓም መመለሱን እንደሰሙ ወደ ማኅበረሰቡ ካስጠሩት በኋላ በመላው እስራኤል ላይ አነገሡት።+ ከይሁዳ ነገድ በስተቀር ከሕዝቡ መሃል የዳዊትን ቤት የተከተለ ማንም አልነበረም።+ 21  ሮብዓም ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ ከእስራኤል ቤት ጋር ተዋግተው ንግሥናውን ለሰለሞን ልጅ ለሮብዓም እንዲያስመልሱ ከመላው የይሁዳ ቤትና ከቢንያም ነገድ የተውጣጡ 180,000 የሠለጠኑ* ተዋጊዎች ወዲያውኑ ሰበሰበ።+ 22  ከዚያም የእውነተኛው አምላክ ቃል የእውነተኛው አምላክ ሰው ወደሆነው ወደ ሸማያህ+ እንዲህ ሲል መጣ፦ 23  “ለይሁዳ ንጉሥ ለሰለሞን ልጅ ለሮብዓም፣ ለይሁዳ ቤት ሁሉ፣ ለቢንያምና ለቀረው ሕዝብ እንዲህ ብለህ ተናገር፦ 24  ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ከወንድሞቻችሁ ከእስራኤላውያን ጋር ለመዋጋት አትውጡ። ይህ እንዲሆን ያደረግኩት እኔ ስለሆንኩ እያንዳንዳችሁ ወደ ቤታችሁ ተመለሱ።”’”+ ስለዚህ የይሖዋን ቃል ሰሙ፤ ይሖዋ እንደነገራቸውም ወደየቤታቸው ተመለሱ። 25  ከዚያም ኢዮርብዓም በኤፍሬም ተራራማ አካባቢ ሴኬምን+ ገንብቶ* በዚያ መኖር ጀመረ። ከዚያ ወጥቶ በመሄድ ጰኑኤልን+ ገነባ።* 26  ኢዮርብዓም በልቡ እንዲህ ሲል አሰበ፦ “እንግዲህ አሁን መንግሥቱ ወደ ዳዊት ቤት ይመለሳል።+ 27  ይህ ሕዝብ በኢየሩሳሌም በሚገኘው የይሖዋ ቤት+ መሥዋዕት ለማቅረብ ወደዚያ መውጣቱን ከቀጠለ የዚህ ሕዝብ ልብ ጌታው ወደሆነው ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ ሮብዓም ይመለሳል። እኔንም ይገድለኛል፤ ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ ሮብዓምም ይመለሳል።” 28  በመሆኑም ንጉሡ ከተማከረ በኋላ ሁለት የወርቅ ጥጃዎችን+ ሠርቶ ሕዝቡን “ወደ ኢየሩሳሌም መውጣት መንገላታት ይሆንባችኋል። እስራኤል ሆይ፣ ከግብፅ ምድር ያወጣህ አምላክህ ይኸውልህ” አለ።+ 29  ከዚያም አንደኛውን በቤቴል+ ሌላኛውን ደግሞ በዳን+ አቆመው። 30  ይህም ለኃጢአት ዳረጋቸው፤+ ሕዝቡም በዳን የሚገኘውን ጥጃ ለማምለክ እስከዚያ ድረስ ይሄድ ነበር። 31  እሱም በኮረብቶቹ ላይ የአምልኮ ቤቶችን ሠራ፤ ከሕዝቡም መካከል ሌዋውያን ያልሆኑ ሰዎችን ካህናት አድርጎ ሾመ።+ 32  በተጨማሪም ኢዮርብዓም በስምንተኛው ወር ከወሩም በ15ኛው ቀን በይሁዳ ይከበር የነበረው ዓይነት በዓል እንዲቋቋም አደረገ።+ ለሠራቸውም ጥጆች በቤቴል+ በሠራው መሠዊያ ላይ መሥዋዕት አቀረበ፤ በቤቴል ለሠራቸው ከፍ ያሉ የማምለኪያ ቦታዎችም ካህናት መደበ። 33  በቤቴል በሠራው መሠዊያም ላይ ራሱ በመረጠው ወር ይኸውም በስምንተኛው ወር በ15ኛው ቀን መባዎችን ማቅረብ ጀመረ፤ ለእስራኤል ሰዎችም በዓል አቋቋመ፤ እንዲሁም መባዎችንና የሚጨሱ መሥዋዕቶችን ለማቅረብ ወደ መሠዊያው ወጣ።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ጨቋኝ።”
ቃል በቃል “ወደየድንኳናቸው።”
ቃል በቃል “የተመረጡ።”
ወይም “ምሽግ አድርጎ በመሥራት።”
ወይም “ምሽግ አድርጎ ሠራ።”