አንደኛ ነገሥት 13:1-34

  • ቤቴል ስለሚገኘው መሠዊያ የተነገረ ትንቢት (1-10)

    • መሠዊያው ተሰነጠቀ (5)

  • የእውነተኛው አምላክ ሰው (11-34)

13  ኢዮርብዓም በመሠዊያው+ አጠገብ የሚጨስ መሥዋዕት ለማቅረብ ቆሞ ሳለ አንድ የአምላክ ሰው+ በይሖዋ ቃል በታዘዘው መሠረት ከይሁዳ ወደ ቤቴል መጣ።  ከዚያም በይሖዋ ቃል በታዘዘው መሠረት መሠዊያውን በመቃወም እንዲህ ሲል ተጣራ፦ “መሠዊያ ሆይ! መሠዊያ ሆይ! ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘እነሆ፣ ኢዮስያስ+ የተባለ ልጅ ለዳዊት ቤት ይወለዳል! እሱም በአንተ ላይ የሚጨስ መሥዋዕት እያቀረቡ ያሉትን ከፍ ያሉ የማምለኪያ ቦታዎች ካህናት በላይህ ይሠዋቸዋል፤ በአንተም ላይ የሰዎችን አጥንት ያቃጥላል።’”+  እሱም በዚያ ቀን እንዲህ በማለት ምልክት* ሰጠ፦ “ይሖዋ የሰጠው ምልክት* ይህ ነው፦ እነሆ፣ መሠዊያው ይሰነጠቃል፤ በላዩም ላይ ያለው አመድ* ይፈስሳል።”  ንጉሡ ኢዮርብዓምም የእውነተኛው አምላክ ሰው በቤቴል የሚገኘውን መሠዊያ በመቃወም የተናገረውን ቃል ሲሰማ እጁን ከመሠዊያው ላይ አንስቶ በመዘርጋት “ያዙት!” አላቸው።+ ወዲያውኑም ወደ እሱ የዘረጋው እጁ ደረቀ፤* እጁንም ሊያጥፈው አልቻለም።+  ከዚያም የእውነተኛው አምላክ ሰው በይሖዋ ቃል ታዞ በሰጠው ምልክት* መሠረት መሠዊያው ተሰነጠቀ፤ አመዱም ከመሠዊያው ላይ ፈሰሰ።  በዚህ ጊዜ ንጉሡ የእውነተኛውን አምላክ ሰው “እባክህ፣ የአምላክህን የይሖዋን ሞገስ እንዳገኝ ለምንልኝ፤ እጄም ወደ ቦታው እንዲመለስ ጸልይልኝ” አለው።+ በዚህ ጊዜ የእውነተኛው አምላክ ሰው የይሖዋን ሞገስ እንዲያገኝ ለመነለት፤ የንጉሡም እጅ ተመልሶ እንደቀድሞው ሆነ።  ከዚያም ንጉሡ የእውነተኛውን አምላክ ሰው “አብረኸኝ ወደ ቤት ሂድና ምግብ ብላ፤ ስጦታም ልስጥህ” አለው።  ሆኖም የእውነተኛው አምላክ ሰው ንጉሡን እንዲህ አለው፦ “የቤትህን ግማሽ ብትሰጠኝ እንኳ ከአንተ ጋር አልሄድም፤ በዚህም ቦታ ምግብ አልበላም፤ ውኃም አልጠጣም።  ምክንያቱም የይሖዋ ቃል ‘ምግብ እንዳትበላ፤ ውኃም እንዳትጠጣ፤ በሄድክበትም መንገድ እንዳትመለስ’ ሲል አዞኛል።” 10  በመሆኑም በሌላ መንገድ ሄደ፤ ወደ ቤቴል በመጣበትም መንገድ አልተመለሰም። 11  በዚህ ጊዜ በቤቴል የሚኖር አንድ አረጋዊ ነቢይ ነበር፤ ልጆቹም ወደ ቤት መጥተው የእውነተኛው አምላክ ሰው በዚያ ቀን በቤቴል ያደረገውን ነገር ሁሉና ለንጉሡ የተናገረውን ቃል ነገሩት። ይህን ለአባታቸው ከተረኩለት በኋላ 12  አባታቸው “ለመሆኑ የሄደው በየት በኩል ነው?” ሲል ጠየቃቸው። ልጆቹም ከይሁዳ የመጣው የእውነተኛው አምላክ ሰው የሄደበትን መንገድ አሳዩት። 13  እሱም ልጆቹን “በሉ አህያውን ጫኑልኝ” አላቸው። እነሱም አህያውን ጫኑለት፤ እሱም አህያው ላይ ተቀመጠ። 14  ከዚያም የእውነተኛውን አምላክ ሰው ተከተለው፤ በአንድ ትልቅ ዛፍ ሥር ተቀምጦም አገኘው። እሱም “ከይሁዳ የመጣኸው የእውነተኛው አምላክ ሰው አንተ ነህ?” አለው፤+ እሱም “አዎ፣ እኔ ነኝ” ሲል መለሰለት። 15  ከዚያም “አብረን ወደ ቤት እንሂድና ምግብ ብላ” አለው። 16  እሱ ግን እንዲህ አለው፦ “ከአንተ ጋር ተመልሼ ልሄድ ወይም ያቀረብክልኝን ግብዣ ልቀበል አልችልም፤ ደግሞም በዚህ ቦታ ከአንተ ጋር ምግብም ሆነ ውኃ አልቀምስም። 17  ምክንያቱም የይሖዋ ቃል ‘እዚያ ምግብ እንዳትበላ፤ ውኃም እንዳትጠጣ። በመጣህበትም መንገድ እንዳትመለስ’ በማለት አዞኛል።” 18  በዚህ ጊዜ አረጋዊው ሰው “እኔም እኮ እንደ አንተው ነቢይ ነኝ፤ አንድ መልአክ ‘ምግብ እንዲበላና ውኃ እንዲጠጣ መልሰህ ወደ ቤትህ አምጣው’ በማለት የይሖዋን ቃል ነግሮኛል” አለው። (እሱም አታለለው።) 19  በመሆኑም እሱ ቤት ምግብ ለመብላትና ውኃ ለመጠጣት አብሮት ተመለሰ። 20  እነሱም በማዕድ ተቀምጠው ሳሉ የይሖዋ ቃል የእውነተኛውን አምላክ ሰው መልሶ ወዳመጣው ነቢይ መጣ፤ 21  ከዚያም ከይሁዳ የመጣውን የእውነተኛውን አምላክ ሰው ጠርቶ እንዲህ አለው፦ “ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘በይሖዋ መመሪያ ላይ ስላመፅክና አምላክህ ይሖዋ የሰጠህን ትእዛዝ ስላልጠበቅክ፣ 22  ከዚህ ይልቅ ምግብ ለመብላትና ውኃ ለመጠጣት ስትል “ምግብ እንዳትበላ፤ ውኃም እንዳትጠጣ” ወደተባልክበት ቦታ ስለተመለስክ ሬሳህ በአባቶችህ የመቃብር ቦታ አይቀበርም።’”+ 23  የእውነተኛው አምላክ ሰውም ከበላና ከጠጣ በኋላ አረጋዊው ነቢይ ከመንገድ መልሶ ላመጣው ለዚያ ነቢይ አህያውን ጫነለት። 24  ከዚያም መንገዱን ቀጠለ፤ ሆኖም አንድ አንበሳ መንገድ ላይ አግኝቶ ገደለው።+ ሬሳውም መንገዱ ላይ ተጋድሞ፣ አህያው ደግሞ አጠገቡ ቆሞ ነበር፤ አንበሳውም ሬሳው አጠገብ ቆሞ ነበር። 25  በዚያ የሚያልፉ ሰዎችም ሬሳው መንገድ ላይ ተጋድሞ፣ አንበሳው ደግሞ አጠገቡ ቆሞ አዩ። ከዚያም መጥተው ይህን ነገር አረጋዊው ነቢይ በሚኖርበት ከተማ አወሩ። 26  ከመንገድ መልሶ ያመጣውም ነቢይ ይህን ሲሰማ ወዲያውኑ “ይህ ሰው በይሖዋ መመሪያ ላይ ያመፀው የእውነተኛው አምላክ ሰው ነው፤+ ይሖዋ በነገረው ቃል መሠረት እንዲቦጫጭቀውና እንዲገድለው ይሖዋ ለአንበሳ አሳልፎ ሰጥቶታል” አለ።+ 27  እሱም ልጆቹን “በሉ አህያውን ጫኑልኝ” አላቸው። እነሱም ጫኑለት። 28  ከዚያም ሄደ፤ ሬሳው መንገድ ላይ ተጋድሞ፣ አህያውና አንበሳውም አጠገቡ ቆመው አገኛቸው። አንበሳው ሬሳውን አልበላውም፤ አህያውንም ቢሆን አልቦጫጨቀውም። 29  ነቢዩም የእውነተኛውን አምላክ ሰው ሬሳ አንስቶ አህያው ላይ ከጫነ በኋላ አልቅሶ ሊቀብረው ስላሰበ ወደሚኖርበት ከተማ ይዞት ተመለሰ። 30  ከዚያም ሬሳውን በራሱ የመቃብር ቦታ ቀበረው፤ እነሱም “ወይኔ ወንድሜን!” እያሉ አለቀሱለት። 31  እሱንም ከቀበረው በኋላ ልጆቹን እንዲህ አላቸው፦ “እኔም ስሞት የእውነተኛው አምላክ ሰው በተቀበረበት የመቃብር ቦታ ቅበሩኝ። አጥንቶቼንም ከአጥንቶቹ አጠገብ ቅበሯቸው።+ 32  በይሖዋ ቃል በታዘዘው መሠረት በቤቴል በሚገኘው መሠዊያና በሰማርያ ከተሞች በሚገኙት ኮረብቶች ላይ ባሉት የአምልኮ ቤቶች+ ሁሉ ላይ የተናገረው ቃል ያለጥርጥር ይፈጸማል።”+ 33  ይህ ሁሉ ከሆነም በኋላ ቢሆን ኢዮርብዓም ከመጥፎ መንገዱ አልተመለሰም፤ ከዚህ ይልቅ ከፍ ላሉት የማምለኪያ ቦታዎች ከሕዝቡ መካከል ካህናት መሾሙን ቀጠለ።+ እንዲሁም ካህን ለመሆን የሚፈልግን ማንኛውንም ሰው “ከፍ ላሉት የማምለኪያ ቦታዎች ካህን ይሁን” በማለት ይሾመው* ነበር።+ 34  ይህም ኃጢአት የኢዮርብዓም+ ቤት ከምድር ገጽ እንዲጠፋና እንዲደመሰስ ምክንያት ሆነ።+

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ተአምራዊ ምልክት።”
ወይም “ተአምራዊ ምልክት።”
ወይም “በስብ የራሰው አመድ።” መሥዋዕት ሆነው በሚቀርቡት እንስሳት ስብ የራሰውን አመድ ያመለክታል።
ወይም “ሽባ ሆነ።”
ወይም “ተአምራዊ ምልክት።”
ቃል በቃል “እጁን ይሞላው።”