ሁለተኛ ሳሙኤል 1:1-27

  • ዳዊት፣ ሳኦል መሞቱን ሰማ (1-16)

  • ዳዊት ለሳኦልና ለልጁ ለዮናታን የተቀኘው የሐዘን እንጉርጉሮ (17-27)

1  ሳኦል ከሞተ በኋላ ዳዊት አማሌቃውያንን ድል አድርጎ* ሲመለስ በጺቅላግ+ ሁለት ቀን ቆየ።  በሦስተኛውም ቀን አንድ ሰው ልብሱን ቀዶና በራሱ ላይ አቧራ ነስንሶ ከሳኦል ሰፈር መጣ። እሱም ዳዊት ጋ ሲደርስ መሬት ላይ ተደፍቶ ሰገደ።  ዳዊትም “ከየት ነው የመጣኸው?” ሲል ጠየቀው፤ እሱም “ከእስራኤል ሰፈር አምልጬ ነው” በማለት መለሰለት።  ዳዊትም “እስቲ የሆነውን ነገር ንገረኝ” አለው። እሱም “ሰዎቹ ከውጊያው ሸሽተዋል፤ ብዙዎቹም ወድቀዋል፤ ሞተዋል። ሳኦልና ልጁ ዮናታንም እንኳ ሞተዋል” አለው።+  ከዚያም ዳዊት ወሬውን ያመጣለትን ወጣት “ለመሆኑ ሳኦልና ልጁ ዮናታን መሞታቸውን እንዴት አወቅክ?” ሲል ጠየቀው።  ወጣቱም እንዲህ አለው፦ “እንደ አጋጣሚ ሆኖ ጊልቦአ+ ተራራ ላይ ነበርኩ፤ እዚያም ሳኦል ጦሩን ተመርኩዞ ቆሞ ነበር፤ ሠረገሎቹና ፈረሰኞቹም ደረሱበት።+  ወደ ኋላም ዞር ብሎ ሲያየኝ ጠራኝ፤ እኔም ‘አቤት!’ አልኩት።  እሱም ‘አንተ ማን ነህ?’ አለኝ፤ እኔም ‘አማሌቃዊ+ ነኝ’ አልኩት።  ከዚያም ‘ሕይወቴ ያላለፈች* ቢሆንም ከባድ ሥቃይ ላይ ስለሆንኩ እባክህ ላዬ ላይ ቁምና ግደለኝ’ አለኝ። 10  በመሆኑም መቼም ቆስሎ ከወደቀ በኋላ እንደማይተርፍ ስላወቅኩ ላዩ ላይ ቆሜ ገደልኩት።+ ከዚያም ራሱ ላይ ያለውን ዘውድና ክንዱ ላይ የነበረውን አምባር ወስጄ ወደ ጌታዬ ይዤ መጣሁ።” 11  በዚህ ጊዜ ዳዊት ልብሱን ቀደደ፤ አብረውት ያሉትም ሰዎች ሁሉ እንደዚሁ አደረጉ። 12  ከዚያም ለሳኦል፣ ለልጁ ለዮናታን፣ ለይሖዋ ሕዝብና ለእስራኤል ቤት+ እስከ ማታ ድረስ ጮኹ፣ አለቀሱ እንዲሁም ጾሙ፤+ በሰይፍ ወድቀዋልና። 13  ዳዊትም ወሬውን ያመጣለትን ወጣት “የየት አገር ሰው ነህ?” አለው። እሱም “የባዕድ አገር ሰው የሆነ የአንድ አማሌቃዊ ልጅ ነኝ” አለው። 14  ከዚያም ዳዊት “ይሖዋ የቀባውን ለመግደል እጅህን ስታነሳ እንዴት አልፈራህም?” አለው።+ 15  ዳዊትም ከወጣቶቹ መካከል አንዱን ጠርቶ “በል ቅረብና ምታው” አለው። እሱም መታው፤ ወጣቱም ሞተ።+ 16  ከዚያም ዳዊት “‘ይሖዋ የቀባውን እኔ ራሴ ገድዬዋለሁ’ በማለት የገዛ አፍህ ስለመሠከረብህ ደምህ በራስህ ላይ ነው” አለው።+ 17  ዳዊትም ለሳኦልና ለልጁ ለዮናታን ይህን የሐዘን እንጉርጉሮ ተቀኘ፤+ 18  እንዲሁም በያሻር መጽሐፍ+ ተጽፎ የሚገኘውን “ቀስት” የተባለውን ሙሾ* የይሁዳ ልጆች እንዲማሩ አዘዘ። 19  “እስራኤል ሆይ፣ ውበት በኮረብቶችህ ላይ ተገድሎ ተጋድሟል።+ ኃያላኑ እንዴት እንዲህ ይውደቁ! 20  ይህን በጌት አትናገሩ፤+በአስቀሎን ጎዳናዎችም ላይ አታውጁ፤አለዚያ የፍልስጤም ሴቶች ልጆች ይደሰታሉ፣የእነዚያ ያልተገረዙ ሰዎች ሴቶች ልጆችም ይፈነድቃሉ። 21  እናንተ የጊልቦአ ተራሮች፣+ጠል አያረስርሳችሁ ወይም ዝናብ አይዝነብባችሁ፣ለቅዱስ መዋጮዎች የሚሆን እህል የሚያበቅሉ ማሳዎችም አይገኙባችሁ፣+በዚያ የኃያላኑ ጋሻ ረክሷልና፣የሳኦልም ጋሻ ከእንግዲህ በዘይት አይወለወልም። 22  ከተገደሉት ሰዎች ደም፣ ከኃያላኑ ስብ፣የዮናታን ቀስት አልተመለሰም፤+የሳኦልም ሰይፍ ድል ሳያደርግ አይመለስም።+ 23  ሳኦልና ዮናታን+ በሕይወት ሳሉ የሚወደዱና የሚደነቁ* ነበሩ፤ሲሞቱም አልተለያዩም።+ ከንስር ይልቅ ፈጣኖች፣+ከአንበሳም ይልቅ ብርቱዎች ነበሩ።+ 24  እናንተ የእስራኤል ሴቶች ልጆች፣የተንቆጠቆጡ ደማቅ ቀይ ልብሶችን ላለበሳችሁ፣ልብሶቻችሁንም በወርቅ ላስጌጠላችሁ ለሳኦል አልቅሱ። 25  ኃያላኑ በጦርነት ላይ እንዴት እንዲህ ይውደቁ! ዮናታን በኮረብቶችህ ላይ ተገድሎ ተጋድሟል!+ 26  ወንድሜ ዮናታን፣ በአንተ የተነሳ ተጨንቄአለሁ፤አንተ በእኔ ዘንድ እጅግ የተወደድክ ነበርክ።+ የአንተ ፍቅር ለእኔ ከሴት ፍቅር ይበልጥ ነበር።+ 27  ኃያላኑ እንዴት እንዲህ ይውደቁ፤የጦር መሣሪያዎቹስ እንዴት እንዲህ ይጥፉ!”

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “መትቶ።”
ወይም “ነፍሴ ገና በውስጤ ያለች።”
ወይም “የሐዘን እንጉርጉሮ።”
ወይም “ደስ የሚሉ።”