ሁለተኛ ሳሙኤል 19:1-43

  • ዳዊት ለአቢሴሎም አለቀሰ (1-4)

  • ኢዮዓብ ዳዊትን ገሠጸው (5-8ሀ)

  • ዳዊት ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ (8ለ-15)

  • ሺምአይ ይቅርታ ጠየቀ (16-23)

  • ሜፊቦስቴ በዳዊት ላይ የፈጸመው በደል እንደሌለ ተረጋገጠ (24-30)

  • ቤርዜሊ የንጉሡን አክብሮት አተረፈ (31-40)

  • በእስራኤልና በይሁዳ ሰዎች መካከል ውዝግብ ተፈጠረ (41-43)

19  ለኢዮዓብ “ንጉሡ ለአቢሴሎም እያለቀሰና እያዘነ ነው” ተብሎ ተነገረው።+  ሕዝቡ ሁሉ ንጉሡ በልጁ ምክንያት ማዘኑን ሲሰማ ያን ዕለት የተገኘው ድል* ወደ ሐዘን ተለወጠ።  በዚያን ቀን ሕዝቡ ከጦርነት በመሸሹ ምክንያት በኀፍረት እንደተሸማቀቀ ሕዝብ ድምፁን አጥፍቶ ወደ ከተማዋ ገባ።+  ንጉሡም ፊቱን ተከናንቦ “ልጄ አቢሴሎም! ልጄ አቢሴሎም፣ ልጄ!” እያለ ድምፁን ከፍ አድርጎ ያለቅስ ነበር።+  ከዚያም ኢዮዓብ ቤቱ ውስጥ ወደነበረው ወደ ንጉሡ ገብቶ እንዲህ አለው፦ “በዛሬው ዕለት የአንተን፣ የወንዶች ልጆችህን፣+ የሴቶች ልጆችህን፣+ የሚስቶችህንና የቁባቶችህን+ ሕይወት* የታደጉትን አገልጋዮችህን ሁሉ አሳፍረሃቸዋል።  አንተ የሚጠሉህን ትወዳለህ፣ የሚወዱህን ደግሞ ትጠላለህ፤ የጦር አለቆችህም ሆኑ አገልጋዮችህ ለአንተ ምንህም እንዳይደሉ ይኸው ዛሬ በግልጽ አሳይተሃል፤ በዛሬው ቀን አቢሴሎም ብቻ በሕይወት ተርፎ እኛ ሁላችን አልቀን ቢሆን ኖሮ ደስ ይልህ እንደነበር እርግጠኛ ነኝ።  በል አሁን ተነስተህ ውጣና አገልጋዮችህን አበረታታቸው፤* ባትወጣ ግን በይሖዋ እምላለሁ፣ ዛሬ አንድም ሰው አብሮህ አያድርም። ይህ ደግሞ ከልጅነትህ አንስቶ እስካሁን ድረስ ከደረሰብህ ጉዳት ሁሉ የከፋ ይሆናል።”  በመሆኑም ንጉሡ ተነስቶ በከተማዋ በር አጠገብ ተቀመጠ፤ ለሕዝቡም ሁሉ “ንጉሡ በሩ አጠገብ ተቀምጧል” ተብሎ ተነገረው። ከዚያም ሕዝቡ ሁሉ ወደ ንጉሡ መጣ። እስራኤላውያን ግን ወደየቤታቸው ሸሽተው ነበር።+  በመላው የእስራኤል ነገዶች መካከል ያለው ሕዝብ እንዲህ በማለት ይከራከር ነበር፦ “ንጉሡ ከጠላቶቻችን አዳነን፤+ ከፍልስጤማውያንም ታደገን፤ አሁን ግን በአቢሴሎም የተነሳ ከአገሩ ሸሽቶ ሄዷል።+ 10  በላያችን እንዲነግሥ የቀባነው+ አቢሴሎም እንደሆነ በውጊያው ሞቷል።+ ታዲያ ንጉሡን ለመመለስ አንድ ነገር የማታደርጉት ለምንድን ነው?” 11  ንጉሥ ዳዊት ለካህናቱ ለሳዶቅና+ ለአብያታር+ እንዲህ የሚል መልእክት ላከባቸው፦ “የይሁዳን ሽማግሌዎች+ እንዲህ በሏቸው፦ ‘እስራኤላውያን በሙሉ የተናገሩት ነገር በቤቱ ውስጥ ወዳለው ወደ ንጉሡ ደርሶ ሳለ እናንተ ንጉሡን ወደ ቤቱ ለመመለስ እንዴት የመጨረሻዎቹ ሰዎች ትሆናላችሁ? 12  እናንተ ወንድሞቼ ናችሁ፤ የአጥንቴ ፍላጭና የሥጋዬ ቁራጭ* ናችሁ። ታዲያ ንጉሡን ለመመለስ እንዴት የመጨረሻዎቹ ሰዎች ትሆናላችሁ?’ 13  አሜሳይንም+ ‘አንተ የአጥንቴ ፍላጭና የሥጋዬ ቁራጭ አይደለህም? ከአሁን ጀምሮ በኢዮዓብ+ ምትክ የሠራዊቴ አለቃ ባትሆን አምላክ እንዲህ ያድርግብኝ፤ ከዚህ የባሰም ያምጣብኝ’ በሉት።” 14  በመሆኑም የይሁዳን ሰዎች ሁሉ ልብ ልክ እንደ አንድ ሰው ልብ ማረከ፤* እነሱም ወደ ንጉሡ “አንተም ሆንክ አገልጋዮችህ በሙሉ ተመለሱ” የሚል መልእክት ላኩበት። 15  ንጉሡም ለመመለስ ጉዞ ጀመረ፤ እስከ ዮርዳኖስም ድረስ መጣ፤ የይሁዳም ሰዎች ንጉሡን ለመቀበልና እስከ ዮርዳኖስ ማዶ ድረስ ለመሸኘት ወደ ጊልጋል+ መጡ። 16  የባሁሪም ሰው የሆነው ቢንያማዊው የጌራ ልጅ ሺምአይ+ ንጉሥ ዳዊትን ለማግኘት ከይሁዳ ሰዎች ጋር በፍጥነት ወረደ፤ 17  ከእሱም ጋር ከቢንያም የመጡ 1,000 ሰዎች ነበሩ። በተጨማሪም የሳኦል ቤት አገልጋይ የሆነው ሲባ+ ከ15 ወንዶች ልጆቹና ከ20 አገልጋዮቹ ጋር በመሆን ከንጉሡ ቀድሞ በፍጥነት ወደ ዮርዳኖስ ወረደ። 18  እሱም* የንጉሡን ቤተሰብ ለማሻገርና ንጉሡ ደስ የሚያሰኘውን ለማድረግ መልካውን* ተሻገረ። የጌራ ልጅ ሺምአይ ግን ንጉሡ ዮርዳኖስን ሊሻገር ሲል በፊቱ ተደፋ። 19  ንጉሡንም እንዲህ አለው፦ “ጌታዬ በደሌን አይቁጠርብኝ፤ ጌታዬ ንጉሡ ከኢየሩሳሌም በወጣበት ቀን አገልጋይህ የፈጸመውን በደል አያስብ።+ ንጉሡም በልቡ አይያዘው፤ 20  ምክንያቱም እኔ አገልጋይህ ኃጢአት እንደሠራሁ በሚገባ አውቃለሁ፤ በመሆኑም ዛሬ ጌታዬን ንጉሡን ወርጄ ለመቀበል ከመላው የዮሴፍ ቤት ቀድሜ መጥቻለሁ።” 21  በዚህ ጊዜ የጽሩያ+ ልጅ አቢሳ+ “ሺምአይ ይሖዋ የቀባውን በመራገም ለፈጸመው በደል ሞት አይገባውም?” አለ።+ 22  ዳዊት ግን እንዲህ አለ፦ “እናንተ የጽሩያ ልጆች፣+ ይህ ጉዳይ ምን ይመለከታችኋልና ነው ዛሬ እኔን ተቃውማችሁ የተነሳችሁት? በዛሬው ዕለት እስራኤል ውስጥ ሰው መገደል ይገባዋል? በእስራኤል ላይ ንጉሥ መሆኔን ያወቅኩት ዛሬ አይደለም?” 23  ንጉሡ አክሎ ሺምአይን “አይዞህ፣ አትሞትም” አለው። ከዚያም ንጉሡ ማለለት።+ 24  የሳኦል የልጅ ልጅ የሆነው ሜፊቦስቴም+ ንጉሡን ለመቀበል ወረደ። እሱም ንጉሡ ከሄደበት ቀን አንስቶ በሰላም እስከተመለሰበት ዕለት ድረስ ለእግሩ ተገቢውን እንክብካቤ አላደረገም፣ ጢሙን አልተከረከመም፤ ልብሱንም አላጠበም። 25  እሱም ንጉሡን ለማግኘት ወደ ኢየሩሳሌም* በመጣ ጊዜ ንጉሡ “ሜፊቦስቴ፣ አብረኸኝ ያልሄድከው ለምንድን ነው?” አለው። 26  በዚህ ጊዜ እንዲህ አለው፦ “ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፣ አገልጋዬ+ አታለለኝ። እኔ አገልጋይህ ሽባ+ ስለሆንኩ ‘በአህያዬ ላይ ተቀምጬ ከንጉሡ ጋር እንድሄድ አህያዬን ጫኑልኝ’ ብዬ ነበር። 27  ሆኖም እሱ በጌታዬ በንጉሡ ፊት የእኔን የአገልጋይህን ስም አጥፍቷል።+ ይሁን እንጂ ጌታዬ ንጉሡ እንደ እውነተኛው አምላክ መልአክ ስለሆነ መልካም መስሎ የታየህን አድርግ። 28  የአባቴ ቤት በሙሉ በንጉሡ በጌታዬ ሞት ሊፈረድበት ይገባ ነበር፤ አንተ ግን አገልጋይህን ከማዕድህ ከሚበሉት አንዱ አደረግከው።+ ታዲያ ንጉሡን ተጨማሪ ነገር የመጠየቅ ምን መብት አለኝ?” 29  ሆኖም ንጉሡ “ለምን ዝም ብለህ ነገር ታስረዝማለህ? እርሻውን አንተና ሲባ እንድትካፈሉ ወስኛለሁ” አለው።+ 30  በዚህ ጊዜ ሜፊቦስቴ ንጉሡን “ጌታዬ ንጉሡ ወደ ቤቱ እንኳን በሰላም ተመለሰ እንጂ እሱ ሁሉንም ይውሰደው” አለው። 31  ከዚያም ጊልያዳዊው ቤርዜሊ+ ንጉሡን ወደ ዮርዳኖስ ለመሸኘት ከሮገሊም ወደ ዮርዳኖስ ወረደ። 32  ቤርዜሊ የ80 ዓመት አረጋዊ ነበር፤ እጅግ ባለጸጋም ስለነበር ንጉሡ በማሃናይም ይኖር በነበረበት ጊዜ ቀለብ አምጥቶለት ነበር።+ 33  በመሆኑም ንጉሡ ቤርዜሊን “አብረኸኝ ተሻገር፤ እኔም በኢየሩሳሌም ቀለብ እሰጥሃለሁ” አለው።+ 34  ቤርዜሊ ግን ንጉሡን እንዲህ አለው፦ “ከንጉሡ ጋር ወደ ኢየሩሳሌም የምወጣው ለየትኛው ዕድሜዬ ብዬ ነው? 35  አሁን የ80 ዓመት ሰው ነኝ።+ ታዲያ መልካምና መጥፎውን መለየት እችላለሁ? እኔ አገልጋይህ የምበላውንና የምጠጣውን ማጣጣም እችላለሁ? ደግሞስ የወንድና የሴት ዘፋኞችን ድምፅ መስማት እችላለሁ?+ ታዲያ አገልጋይህ ለጌታዬ ለንጉሡ ለምን ተጨማሪ ሸክም ይሆናል? 36  አገልጋይህ ንጉሡን እስከ ዮርዳኖስ ድረስ መሸኘት ከቻለ ይበቃዋል። ታዲያ ንጉሡ ይህን ወሮታ የሚመልስልኝ ለምንድን ነው? 37  እባክህ እኔ አገልጋይህ ልመለስና በገዛ ከተማዬ በአባቴና በእናቴ መቃብር አጠገብ ልሙት።+ ሆኖም አገልጋይህ ኪምሃም+ ይኸውልህ። እሱ ከጌታዬ ከንጉሡ ጋር ይሻገር፤ አንተም መልካም መስሎ የታየህን አድርግለት።” 38  በመሆኑም ንጉሡ “እንግዲያው ኪምሃም አብሮኝ ይሻገራል፤ እኔም መልካም መስሎ የታየህን አደርግለታለሁ፤ ለአንተም የምትጠይቀኝን ማንኛውንም ነገር አደርግልሃለሁ” አለው። 39  በዚህ ጊዜ ሕዝቡ ሁሉ ዮርዳኖስን መሻገር ጀመረ፤ ንጉሡም ሊሻገር ሲል ቤርዜሊን ስሞ ባረከው፤+ ቤርዜሊም ወደ ቤቱ ተመለሰ። 40  ንጉሡ ወደ ጊልጋል+ ሲሻገር ኪምሃምም አብሮት ተሻገረ። እንዲሁም የይሁዳ ሰዎች በሙሉና ግማሹ የእስራኤል ሕዝብ ንጉሡን አሻገሩት።+ 41  ከዚያም የእስራኤል ሰዎች ሁሉ ወደ ንጉሡ ቀርበው “ወንድሞቻችን የሆኑት የይሁዳ ሰዎች ሹልክ ብለው ይዘውህ በመሄድ ንጉሡንና ቤተሰቡን ከዳዊት ሰዎች ሁሉ ጋር ዮርዳኖስን ያሻገሩት ለምንድን ነው?” አሉት።+ 42  በዚህ ጊዜ የይሁዳ ሰዎች ሁሉ የእስራኤልን ሰዎች “ይህን ያደረግነው ንጉሡ ዘመዳችን ስለሆነ ነው።+ ታዲያ ይህ እናንተን ያስቆጣችሁ ለምንድን ነው? በንጉሡ ወጪ የበላነው ነገር አለ? ወይስ ስጦታ መጥቶልን ያውቃል?” አሏቸው። 43  ሆኖም የእስራኤል ሰዎች የይሁዳን ሰዎች እንዲህ አሏቸው፦ “እኛ እኮ ከንጉሡ አሥር እጅ ድርሻ አለን፤ ስለሆነም በዳዊት ላይ ከእናንተ የበለጠ መብት ያለን እኛ ነን። ታዲያ የናቃችሁን ለምንድን ነው? ንጉሣችንን ለመመለስ ቅድሚያ ሊሰጠን አይገባም ነበር?” ይሁንና ከእስራኤል ሰዎች ቃል ይልቅ የይሁዳ ሰዎች ቃል አሸነፈ።*

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “የተገኘው መዳን።”
ወይም “ነፍስ።”
ቃል በቃል “ለአገልጋዮችህ ልብ ተናገር።”
ወይም “የሥጋ ዘመዶቼ።”
ቃል በቃል “አዘነበለ።”
ወንዝ ማቋረጥ የሚቻልበት ጥልቀት የሌለው የወንዝ ክፍል።
“እነሱም” ማለትም ሊሆን ይችላል።
“ከኢየሩሳሌም” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “ኃይለኛ ነበር።”