ለቆሮንቶስ ሰዎች የተጻፈ ሁለተኛው ደብዳቤ 11:1-33

  • ጳውሎስና ምርጦቹ ሐዋርያት (1-15)

  • ጳውሎስ ሐዋርያ ሆኖ ሲያገለግል ያጋጠሙት መከራዎች (16-33)

11  በመጠኑ ምክንያታዊነት ቢጎድለኝ እንድትታገሡኝ እፈልጋለሁ። ደግሞም እየታገሣችሁኝ ነው!  በአምላክ ቅንዓት እቀናላችኋለሁና፤ እኔ ራሴ እንደ አንዲት ንጽሕት ድንግል ለክርስቶስ አቀርባችሁ ዘንድ ለአንድ ባል አጭቻችኋለሁ።+  ሆኖም እባቡ ሔዋንን በተንኮሉ እንዳታለላት+ ሁሉ እናንተም አስተሳሰባችሁ ተበላሽቶ ለክርስቶስ ልታሳዩ የሚገባውን ቅንነትና ንጽሕና በሆነ መንገድ እንዳታጡ እፈራለሁ።+  አንድ ሰው መጥቶ እኛ የሰበክንላችሁን ሳይሆን ሌላ ኢየሱስ ቢሰብክላችሁ ወይም ከተቀበላችሁት መንፈስ የተለየ ዓይነት መንፈስ ቢያመጣ ወይም ከተቀበላችሁት ምሥራች የተለየ ሌላ ምሥራች ቢናገር+ እንዲህ ያለውን ሰው በቸልታ ታልፉታላችሁ ማለት ነው።  እኔ ከእናንተ የተራቀቁ ሐዋርያት በምንም ነገር የማንስ አይመስለኝም።+  የተዋጣልኝ ተናጋሪ ባልሆን እንኳ+ እውቀት አይጎድለኝም፤ ይህን በሁሉም መንገድ እንዲሁም በሁሉም ነገር አሳይተናችኋል።  ወይስ እናንተ ከፍ እንድትሉ ራሴን ዝቅ አድርጌ የአምላክን ምሥራች ለእናንተ ያለዋጋ በደስታ መስበኬ እንደ ኃጢአት ተቆጥሮብኝ ይሆን?+  እናንተን ለማገልገል ከሌሎች ጉባኤዎች ቁሳዊ እርዳታ በመቀበሌ እነሱን አራቁቻለሁ።+  ከእናንተ ጋር ሳለሁ ተቸግሬ በነበረበት ጊዜ ከመቄዶንያ የመጡት ወንድሞች የጎደለኝን ነገር በሙሉ በሚገባ ስላሟሉልኝ ለማንም ሸክም አልሆንኩም።+ አዎ፣ እስካሁን ድረስ በእናንተ ላይ በምንም መንገድ ሸክም አልሆንኩም፤ ወደፊትም ሸክም አልሆንም።+ 10  የክርስቶስ እውነት በውስጤ እስካለ ድረስ በአካይያ ክልሎች ሁሉ በዚህ ነገር እንዳልኩራራ ምንም ነገር ሊያግደኝ አይችልም።+ 11  ይህን ያደረግኩት ለምንድን ነው? ስለማልወዳችሁ ነው? እንደምወዳችሁ አምላክ ያውቃል። 12  ይሁንና ከእኛ ጋር እኩል ለመሆን የሚፈልጉትና እኛም ሐዋርያት ነን ብለው የሚኩራሩት ሰዎች ለዚህ የሚሆን መሠረት* እንዳያገኙ አሁን እያደረግኩት ያለሁትን ወደፊትም አደርጋለሁ።+ 13  እንዲህ ያሉት ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት ለመምሰል ራሳቸውን የሚለውጡ ሐሰተኛ ሐዋርያትና አታላይ ሠራተኞች ናቸውና።+ 14  ይህም ምንም አያስደንቅም፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃን መልአክ ለመምሰል ራሱን ይለዋውጣልና።+ 15  ስለዚህ አገልጋዮቹም የጽድቅ አገልጋዮች ለመምሰል ራሳቸውን ቢለዋውጡ ምንም አያስገርምም። ሆኖም ፍጻሜያቸው እንደ ሥራቸው ይሆናል።+ 16  አሁንም ዳግመኛ እናገራለሁ፦ ማንም ሰው ምክንያታዊ እንዳልሆንኩ አድርጎ አያስብ። እንደዚያ አድርጋችሁ የምትመለከቱኝ ከሆነ ግን እኔም እንደ እነሱ በመጠኑ መኩራራት እንድችል ምክንያታዊነት እንደሚጎድለው ሰው አድርጋችሁ ተቀበሉኝ። 17  እንደዚህ የምናገረው የጌታን ምሳሌ በመከተል ሳይሆን ምክንያታዊ ያልሆነ ሰው እንደሚያደርገው በኩራትና በትምክህት ነው። 18  ብዙዎች በሥጋዊ ነገር ስለሚኩራሩ* እኔም እኩራራለሁ። 19  እናንተ በጣም “ምክንያታዊ” ስለሆናችሁ ምክንያታዊ ያልሆኑ ሰዎችን በደስታ ትታገሣላችሁ። 20  እንዲያውም ማንም እንደ ባሪያ ቢያደርጋችሁ፣ ማንም ንብረታችሁን ሙልጭ አድርጎ ቢወስድባችሁ፣ ማንም ያላችሁን ቢቀማችሁ፣ ማንም ራሱን ከፍ ከፍ ቢያደርግባችሁ ወይም ማንም በጥፊ ቢመታችሁ ትታገሣላችሁ። 21  ይህን መናገር ለእኛ አሳፋሪ ነው፤ ምክንያቱም አንዳንዶች በሥልጣናችን በአግባቡ መጠቀም የማንችል ደካሞች እንደሆን አድርገው ሊያስቡ ይችላሉ። ሆኖም ምክንያታዊነት እንደሚጎድለው ሰው ልናገርና ማንም ሰው በሆነ ነገር የልብ ልብ የሚሰማው ከሆነ እኔም የልብ ልብ ሊሰማኝ ይችላል። 22  ዕብራውያን ናቸው? እኔም ነኝ።+ እስራኤላውያን ናቸው? እኔም ነኝ። የአብርሃም ዘር ናቸው? እኔም ነኝ።+ 23  የክርስቶስ አገልጋዮች ናቸው? እንደ እብድ ሰው ልናገርና እኔ ከሁሉ በላቀ ደረጃ የክርስቶስ አገልጋይ ነኝ፦ ከሁሉም ይበልጥ ሠርቻለሁ፣+ ብዙ ጊዜ ታስሬአለሁ፣+ ብዙ ጊዜ ተደብድቤአለሁ እንዲሁም ብዙ ጊዜ ሞት አፋፍ ደርሻለሁ።+ 24  አይሁዳውያን ለ40 ጅራፍ አንድ የቀረው ግርፋት አምስት ጊዜ ገርፈውኛል፤+ 25  ሦስት ጊዜ በዱላ ተደብድቤአለሁ፤+ አንድ ጊዜ በድንጋይ ተወግሬአለሁ፤+ ሦስት ጊዜ የመርከብ መሰበር አደጋ አጋጥሞኛል፤+ አንድ ሌሊትና አንድ ቀን በባሕር ላይ አሳልፌአለሁ፤ 26  ብዙ ጊዜ ተጉዣለሁ፤ ደግሞም በወንዝ ሙላት ለሚመጣ አደጋ፣ ዘራፊዎች ለሚያደርሱት አደጋ፣ የገዛ ወገኖቼ ለሚያደርሱት አደጋ፣+ ከአሕዛብ ለሚሰነዘር አደጋ፣+ በከተማ፣+ በምድረ በዳና በባሕር ላይ ለሚያጋጥም አደጋ እንዲሁም በሐሰተኛ ወንድሞች መካከል ለሚያጋጥም አደጋ ተጋልጬ ነበር፤ 27  ብዙ ጥሬአለሁ፤ ብዙ ደክሜአለሁ፤ ብዙ ጊዜ እንቅልፍ ሳልተኛ አድሬአለሁ፤+ ተርቤአለሁ፤ ተጠምቻለሁ፤+ ብዙ ጊዜ ምግብ በማጣት ተቸግሬአለሁ፤+ በብርድ ተቆራምጃለሁ፤ በልብስ እጦትም ተቸግሬአለሁ። 28  ከእነዚህ ውጫዊ ችግሮች በተጨማሪ ዕለት ዕለት የሚያስጨንቀኝ* የጉባኤዎች ሁሉ ሐሳብ ነው።+ 29  ድካም የሚሰማው አለ? እኔስ ብሆን ድካም አይሰማኝም? የተሰናከለ አለ? ይህ እኔን በጣም አያናድደኝም? 30  መኩራራት ካስፈለገ ድክመቴን በሚያሳዩ ነገሮች እኩራራለሁ። 31  ለዘላለም የሚመሰገነው የጌታ ኢየሱስ አምላክና አባት እየዋሸሁ እንዳልሆነ ያውቃል። 32  በደማስቆ የንጉሥ አሬጣስ የበታች የሆነው ገዢ ሊይዘኝ ፈልጎ የደማስቆ ሰዎችን ከተማ ያስጠብቅ ነበር፤ 33  ሆኖም በከተማዋ ግንብ ላይ በሚገኘው መስኮት በኩል በቅርጫት አውርደውኝ+ ከእጁ አመለጥኩ።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ሰበብ።”
በሰብዓዊ ነገር መኩራራትን ያመለክታል።
ወይም “በየዕለቱ ጫና የሚፈጥርብኝ።”