ለቆሮንቶስ ሰዎች የተጻፈ ሁለተኛው ደብዳቤ 13:1-14

  • መጨረሻ ላይ የሰጠው ማስጠንቀቂያና ማሳሰቢያ (1-14)

    • ‘በእምነት ውስጥ መሆናችሁን ለማረጋገጥ ራሳችሁን ፈትሹ’ (5)

    • ‘መስተካከላችሁንና በሐሳብ መስማማታችሁን ቀጥሉ’ (11)

13  ወደ እናንተ ለመምጣት ሳስብ ይህ ሦስተኛ ጊዜዬ ነው። “ማንኛውም ጉዳይ የሚጸናው ሁለት ወይም ሦስት ምሥክሮች በሚሰጡት የምሥክርነት ቃል* ነው።”+  ምንም እንኳ አሁን ከእናንተ ርቄ ያለሁ ቢሆንም ለሁለተኛ ጊዜ አብሬያችሁ እንዳለሁ አድርጋችሁ በማሰብ ቃሌን ተቀበሉ። ደግሞም ዳግመኛ ከመጣሁ ማንንም ሳልገሥጽ እንደማላልፍ ከዚህ በፊት ኃጢአት የሠሩትንም ሆነ የተቀሩትን ሁሉ አስቀድሜ አስጠነቅቃለሁ፤  ይህም የሆነው በእናንተ መካከል በድካም ሳይሆን በኃይል የሚሠራው ክርስቶስ በእኔ አማካኝነት እንደሚናገር የሚያሳይ ማስረጃ ስለፈለጋችሁ ነው።  እርግጥ ነው፣ እሱ በእንጨት ላይ የተሰቀለው በድካም የተነሳ* ነው፤ ይሁንና በአምላክ ኃይል የተነሳ ሕያው ሆኗል።+ እርግጥ እኛም ከእሱ ጋር ደካሞች ነን፤ ሆኖም በእናንተ ላይ እየሠራ ባለው የአምላክ ኃይል+ ከእሱ ጋር እንኖራለን።+  በእምነት ውስጥ መሆናችሁን ለማረጋገጥ ዘወትር ራሳችሁን ፈትሹ፤ ማንነታችሁን ለማወቅ ዘወትር ራሳችሁን መርምሩ።+ ተቀባይነት አጥታችሁ ካልሆነ በስተቀር ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናንተ ጋር አንድነት እንዳለው አትገነዘቡም?  እኛ ግን ተቀባይነት ያለን መሆናችንን እንደምትገነዘቡ ተስፋ አደርጋለሁ።  መጥፎ ነገር እንዳትሠሩ ወደ አምላክ እንጸልያለን፤ ይህን የምናደርገው እኛ ተቀባይነት ያለን ሆነን እንድንታይ አይደለም፤ ከዚህ ይልቅ እኛ ተቀባይነት ያላገኘን መስለን ብንታይም እንኳ እናንተ መልካም የሆነውን ነገር እንድታደርጉ ነው።  እኛ ለእውነት የቆምን ነን እንጂ እውነትን የሚጻረር ምንም ነገር ማድረግ አንችልምና።  እኛ በደከምንበት ጊዜ ሁሉ እናንተ ብርቱዎች ብትሆኑ ምንጊዜም ደስተኞች ነን። ደግሞም መስተካከላችሁን እንድትቀጥሉ እንጸልያለን። 10  ከእናንተ ርቄ ሳለሁ እነዚህን ነገሮች የምጽፍላችሁ በመካከላችሁ በምሆንበት ጊዜ ጠበቅ ያለ እርምጃ እንዳልወስድ ነው፤ ጌታ ሥልጣን የሰጠኝ+ እናንተን ለማነጽ እንጂ ለማፍረስ አይደለም። 11  በተረፈ ወንድሞች፣ መደሰታችሁን፣ መስተካከላችሁን፣ ማጽናኛ መቀበላችሁን፣+ በሐሳብ መስማማታችሁንና+ በሰላም መኖራችሁን ቀጥሉ፤+ የፍቅርና የሰላም አምላክም+ ከእናንተ ጋር ይሆናል። 12  እርስ በርስ በመሳሳም* ሰላምታ ተለዋወጡ። 13  ቅዱሳን ሁሉ ሰላምታ ያቀርቡላችኋል። 14  የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና የአምላክ ፍቅር እንዲሁም በጋራ የምንቀበለው መንፈስ ቅዱስ ከሁላችሁ ጋር ይሁን።

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “በሁለት ወይም በሦስት ምሥክሮች አፍ።”
ሰው በመሆኑ የተነሳ።
ቃል በቃል “በተቀደሰ አሳሳም።”