ለተሰሎንቄ ሰዎች የተጻፈ ሁለተኛው ደብዳቤ 3:1-18

  • “መጸለያችሁን አታቋርጡ” (1-5)

  • ሥርዓት በጎደለው መንገድ እንዳይመላለሱ የተሰጠ ማስጠንቀቂያ (6-15)

  • የስንብት ቃላት (16-18)

3  በመጨረሻም ወንድሞች፣ በእናንተ ዘንድ እንደሆነው ሁሉ የይሖዋ* ቃል በፍጥነት መስፋፋቱን እንዲቀጥልና+ እንዲከበር ስለ እኛ መጸለያችሁን አታቋርጡ፤+  ደግሞም ከመጥፎና ከክፉ ሰዎች እንድንድን+ ጸልዩልን፤ እምነት ሁሉም ሰው የሚኖረው ነገር አይደለምና።+  ጌታ ግን ታማኝ ነው፤ እሱ ያጠነክራችኋል፤ እንዲሁም ከክፉው ይጠብቃችኋል።  ከዚህም በላይ እኛ የጌታ ተከታዮች እንደመሆናችን መጠን፣ ያዘዝናችሁን እያደረጋችሁ እንዳለና ወደፊትም ማድረጋችሁን እንደምትቀጥሉ በእናንተ እንተማመናለን።  አምላክን እንድትወዱና+ ክርስቶስን በጽናት+ እንድትከተሉ ጌታ ልባችሁን በትክክለኛው አቅጣጫ መምራቱን ይቀጥል።  ወንድሞች፣ በሥርዓት ከማይሄድና+ ከእኛ የተቀበላችሁትን* ወግ* ከማይከተል+ ማንኛውም ወንድም እንድትርቁ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እናዛችኋለን።  የእኛን አርዓያ እንዴት መከተል እንዳለባችሁ እናንተ ራሳችሁ ታውቃላችሁ፤+ ምክንያቱም በመካከላችሁ ሳለን ሥርዓት በጎደለው መንገድ አልተመላለስንም፤  እንዲሁም የማንንም ምግብ በነፃ አልበላንም።+ እንዲያውም ብዙ ወጪ በማስወጣት በማናችሁም ላይ ሸክም ላለመሆን ሌት ተቀን በመሥራት እንደክምና እንለፋ ነበር።+  ይህን ያደረግነው የእኛን አርዓያ እንድትከተሉ+ ራሳችንን ለእናንተ ምሳሌ አድርገን ለማቅረብ ብለን እንጂ ሥልጣን ሳይኖረን ቀርቶ አይደለም።+ 10  እንዲያውም ከእናንተ ጋር በነበርንበት ጊዜ “መሥራት የማይፈልግ ሁሉ አይብላ” የሚል ትእዛዝ ሰጥተናችሁ ነበር።+ 11  አንዳንዶች ሥራ ፈት በመሆን በማይመለከታቸው ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ+ ሥርዓት በጎደለው መንገድ በመካከላችሁ እንደሚመላለሱ እንሰማለንና።+ 12  እንዲህ ያሉ ሰዎች አርፈው ሥራቸውን በመሥራት በድካማቸው ያገኙትን እንዲበሉ በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እናዛቸዋለን፤ እንዲሁም አጥብቀን እንመክራቸዋለን።+ 13  እናንተ ግን ወንድሞች፣ መልካም የሆነውን ከማድረግ አትታክቱ። 14  ሆኖም በዚህ ደብዳቤ አማካኝነት ላስተላለፍነው ቃል የማይታዘዝ ሰው ቢኖር ይህን ሰው ምልክት አድርጉበት፤* ያፍርም ዘንድ ከእሱ ጋር አትግጠሙ።+ 15  ይሁን እንጂ እንደ ጠላት አትመልከቱት፤ ከዚህ ይልቅ እንደ ወንድም አጥብቃችሁ መምከራችሁን ቀጥሉ።+ 16  የሰላም ጌታ ራሱ በሁሉም መንገድ ዘወትር ሰላም ይስጣችሁ።+ ጌታ ከሁላችሁም ጋር ይሁን። 17  እኔ ጳውሎስ በገዛ እጄ የጻፍኩላችሁ ሰላምታ ይድረሳችሁ፤+ ይህ የእጅ ጽሑፍ የደብዳቤዎቼ ሁሉ መለያ ነው፤ አጻጻፌ እንዲህ ነው። 18  የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከሁላችሁም ጋር ይሁን።

የግርጌ ማስታወሻ

ከተጨማሪው መረጃ ላይ ሀ5ን ተመልከት።
“ከእኛ የተቀበሉትን” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “መመሪያ፤ ትምህርት።”
ወይም “በትኩረት ተከታተሉት።”