ሁለተኛ ነገሥት 4:1-44

  • ኤልሳዕ የመበለቷ ዘይት ከማሰሮው እንዳያልቅ አደረገ (1-7)

  • አንዲት ሹነማዊት ኤልሳዕን አስተናገደችው (8-16)

  • ሴትየዋ ልጅ በመውለድ ተባረከች፤ ልጇ ሞተ (17-31)

  • ኤልሳዕ ልጇን ከሞት አስነሳላት (32-37)

  • “ድስቱ ውስጥ ገዳይ መርዝ አለ” (38-41)

  • ኤልሳዕ በጥቂት ዳቦ ብዙ ሰው መገበ (42-44)

4  ከነቢያት ልጆች+ መካከል የአንዱ ሚስት ወደ ኤልሳዕ መጥታ እንዲህ ስትል ጮኸች፦ “አገልጋይህ ባለቤቴ ሞቷል፤ አገልጋይህ ምንጊዜም ይሖዋን የሚፈራ ሰው እንደነበር በሚገባ ታውቃለህ።+ አሁን ግን አንድ አበዳሪ መጥቶ ሁለቱንም ልጆቼን ባሪያዎቹ አድርጎ ሊወስዳቸው ነው።”  በዚህ ጊዜ ኤልሳዕ “ታዲያ ምን እንዳደርግልሽ ትፈልጊያለሽ? ንገሪኝ፣ ቤት ውስጥ ምን አለሽ?” አላት። እሷም “አገልጋይህ ከአንድ ማሰሮ ዘይት በስተቀር ቤት ውስጥ ምንም ነገር የላትም”+ ብላ መለሰችለት።  ከዚያም እንዲህ አላት፦ “እንግዲያው ሂጂና ከጎረቤቶችሽ ሁሉ ባዶ ዕቃዎች ለምኚ። የቻልሽውን ያህል ብዙ ዕቃ ለምኚ።  ከዚያም ገብተሽ በሩን በአንቺና በልጆችሽ ላይ ዝጊው። ዕቃዎቹንም ሁሉ በዘይት ሙዪ፤ የሞሉትንም ለብቻ አስቀምጫቸው።”  እሷም ወጥታ ሄደች። በሩን በራሷና በልጆቿ ላይ ከዘጋች በኋላ ልጆቿ ዕቃዎቹን ሲያቀርቡላት እሷ ትቀዳባቸው ጀመር።+  ዕቃዎቹ ሲሞሉ ከልጆቿ መካከል አንዱን “ሌላ ዕቃ አምጣልኝ”+ አለችው። እሱ ግን “የቀረ ዕቃ የለም” አላት። በዚህ ጊዜ ዘይቱ መውረዱን አቆመ።+  እሷም ሄዳ ለእውነተኛው አምላክ ሰው ነገረችው፤ እሱም “ሂጂ፤ ዘይቱን ሸጠሽ ዕዳሽን ክፈዪ፤ የተረፈው ደግሞ ለአንቺና ለልጆችሽ መተዳደሪያ ይሁን” አላት።  አንድ ቀን ኤልሳዕ ወደ ሹነም+ ሄደ፤ በዚያም አንዲት ታዋቂ ሴት ነበረች፤ እሷም ምግብ እንዲበላ አጥብቃ ለመነችው።+ እሱም በዚያ ባለፈ ቁጥር ምግብ ለመብላት ወደዚያ ጎራ ይል ነበር።  በመሆኑም ሴትየዋ ባሏን እንዲህ አለችው፦ “ይህ በየጊዜው በዚህ መንገድ የሚያልፈው ሰው ቅዱስ የአምላክ ሰው እንደሆነ አውቃለሁ። 10  እባክህ በሰገነቱ ላይ ትንሽ ክፍል+ ሠርተን አልጋ፣ ጠረጴዛ፣ ወንበርና መቅረዝ እናስገባለት። ከዚያም ወደ እኛ በሚመጣበት ጊዜ ሁሉ እዚያ ማረፍ ይችላል።”+ 11  ኤልሳዕም አንድ ቀን ወደዚያ መጣ፤ ጋደም ለማለትም በሰገነቱ ላይ ወዳለው ክፍል ሄደ። 12  ከዚያም አገልጋዩን ግያዝን+ “እስቲ ሹነማዊቷን+ ሴት ጥራት” አለው። እሱም ጠራት፤ እሷም መጥታ ፊቱ ቆመች። 13  ከዚያም ኤልሳዕ ግያዝን እንዲህ አለው፦ “እባክህ እንዲህ በላት፦ ‘እንግዲህ ለእኛ ስትዪ ብዙ ተቸግረሻል።+ ታዲያ ምን እንዲደረግልሽ ትፈልጊያለሽ?+ ንጉሡን ወይም የሠራዊቱን አለቃ የማነጋግርልሽ ነገር አለ?’”+ እሷ ግን “እኔ እኮ የምኖረው በገዛ ወገኖቼ መካከል ነው” ብላ መለሰች። 14  እሱም “ታዲያ ምን ቢደረግላት ይሻላል?” አለ። ግያዝም “ለነገሩማ ሴትየዋ ወንድ ልጅ የላትም፤+ ባሏ ደግሞ አርጅቷል” አለው። 15  ኤልሳዕም ወዲያውኑ “በል ጥራት” አለው። እሱም ጠራት፤ እሷም በራፉ ላይ ቆመች። 16  ከዚያም “የዛሬ ዓመት በዚሁ ጊዜ ወንድ ልጅ ትታቀፊያለሽ” አላት።+ እሷ ግን “የእውነተኛው አምላክ ሰው ጌታዬ ሆይ፣ ይሄማ አይሆንም! አገልጋይህን መዋሸት እንዳይሆንብህ” አለችው። 17  ይሁንና ሴትየዋ ፀነሰች፤ ኤልሳዕ በነገራትም መሠረት በቀጣዩ ዓመት በዚያው ጊዜ ወንድ ልጅ ወለደች። 18  ልጁም አደገ፤ ከዚያም አንድ ቀን ከአጫጆቹ ጋር ወደነበረው ወደ አባቱ ወጣ። 19  አባቱንም “ራሴን! ወይኔ ራሴን!” አለው። ከዚያም አባቱ አገልጋዩን “ተሸክመህ ወደ እናቱ ውሰደው” አለው። 20  እሱም ተሸክሞ ወደ እናቱ ወሰደው፤ ልጁም እስከ እኩለ ቀን ድረስ እናቱ ጭን ላይ ተቀመጠ፤ ከዚያም ሞተ።+ 21  እሷም ወደ ላይ ወጥታ ልጁን በእውነተኛው አምላክ ሰው አልጋ+ ላይ አስተኛችው፤ በሩንም ዘግታ ሄደች። 22  ባሏንም ጠርታ “እባክህ አንድ አገልጋይና አንድ አህያ ላክልኝና ወደ እውነተኛው አምላክ ሰው በፍጥነት ደርሼ ልመለስ” አለችው። 23  እሱ ግን “ዛሬ ወደ እሱ መሄድ ለምን አስፈለገሽ? አዲስ ጨረቃ+ ወይም ሰንበት አይደለም” አላት። እሷ ግን “ግድ የለም፣ ደርሼ ልምጣ” አለችው። 24  ስለዚህ አህያዋን ከጫነች በኋላ አገልጋይዋን “ቶሎ ቶሎ ሂድ። እኔ ቀስ በል እስካላልኩህ ድረስ ለእኔ ብለህ ፍጥነትህን እንዳትቀንስ” አለችው። 25  በመሆኑም በቀርሜሎስ ተራራ ወደሚገኘው ወደ እውነተኛው አምላክ ሰው ሄደች። የእውነተኛውም አምላክ ሰው ከሩቅ እንዳያት አገልጋዩን ግያዝን እንዲህ አለው፦ “ተመልከት! ሹነማዊቷ ሴት ያቻትና። 26  እባክህ ሮጠህ ወደ እሷ ሂድና ‘ምነው፣ ደህና አይደለሽም? ባልሽ ደህና አይደለም እንዴ? ልጁስ ደህና አይደለም?’ በላት።” እሷም “ሁሉም ነገር ደህና ነው” አለች። 27  ተራራው ላይ ወዳለው ወደ እውነተኛው አምላክ ሰው እንደደረሰች እግሩ ላይ ተጠመጠመች።+ በዚህ ጊዜ ግያዝ ሊያስለቅቃት ሲመጣ የእውነተኛው አምላክ ሰው “ተዋት፣ እጅግ ተጨንቃለች፤* ይሖዋም ነገሩን ከእኔ ደብቆታል፤ የነገረኝ ነገር የለም” አለው። 28  እሷም “ለመሆኑ ጌታዬ ልጅ እንዲሰጠኝ ጠይቄ ነበር? ደግሞስ ‘የማይሆን ተስፋ አትስጠኝ’ አላልኩም?” አለችው።+ 29  እሱም ወዲያውኑ ግያዝን “ልብስህን ወገብህ ላይ ታጠቅ፤+ በትሬን ያዝና ሩጥ። መንገድ ላይ ሰው ብታገኝ ሰላም አትበል፤ ማንም ሰው ሰላም ቢልህም መልስ አትስጠው። ሂድና በትሬን በልጁ ፊት ላይ አድርገው” አለው። 30  በዚህ ጊዜ የልጁ እናት “ሕያው በሆነው በይሖዋና በሕያውነትህ* እምላለሁ፣ ፈጽሞ ትቼህ አልሄድም” አለችው።+ ስለሆነም ተነስቶ አብሯት ሄደ። 31  ግያዝ ቀድሟቸው በመሄድ በትሩን በልጁ ፊት ላይ አደረገው፤ ሆኖም ድምፅም ሆነ ምላሽ አልነበረም።+ እሱም ወደ ኤልሳዕ ተመልሶ በመምጣት “ልጁ አልነቃም” አለው። 32  ኤልሳዕ ወደ ቤት ሲገባ ልጁ ሞቶ በእሱ አልጋ ላይ ተጋድሞ አገኘው።+ 33  ከዚያም ወደ ውስጥ ገብቶ በሩን በራሱና በልጁ ላይ ከዘጋ በኋላ ወደ ይሖዋ መጸለይ ጀመረ።+ 34  ከዚያም አልጋው ላይ ወጥቶ ልጁ ላይ በመተኛት አፉን በአፉ፣ ዓይኑን በዓይኑ እንዲሁም መዳፉን በመዳፉ ላይ አድርጎ ላዩ ላይ ተደፋበት፤ የልጁም ሰውነት መሞቅ ጀመረ።+ 35  ኤልሳዕ ተነስቶ ቤቱ ውስጥ ወዲያ ወዲህ ይል ጀመር፤ ደግሞም እንደገና አልጋው ላይ ወጥቶ ላዩ ላይ ተደፋበት። ልጁም ሰባት ጊዜ ካስነጠሰው በኋላ ዓይኖቹን ገለጠ።+ 36  ኤልሳዕም ግያዝን ጠርቶ “ሹነማዊቷን ሴት ጥራት” አለው። እሱም ጠራት፤ እሷም ወደ እሱ ገባች። ከዚያም ኤልሳዕ “ልጅሽን አንሺው” አላት።+ 37  እሷም ገብታ እግሩ ሥር በመውደቅ ወደ መሬት ለጥ ብላ እጅ ነሳች፤ ልጇንም አንስታ ወጣች። 38  ኤልሳዕ ወደ ጊልጋል ሲመለስ በምድሪቱ ላይ ረሃብ ነበር።+ የነቢያት ልጆች+ በፊቱ ተቀምጠው ነበር፤ አገልጋዩንም+ “ትልቁን ድስት ጣደውና ለነቢያት ልጆች ወጥ ሥራላቸው” አለው። 39  አንድ ሰው ቅጠላ ቅጠል ለማምጣት ወደ ሜዳ ወጣ፤ እሱም ዱር በቀል ሐረግ አገኘ፤ ከሐረጉም ላይ የዱር ቅል ለቅሞ በልብሱ ሙሉ ይዞ ተመለሰ። ከዚያም ምንነታቸውን ሳያውቅ ከትፎ ድስቱ ውስጥ ጨመራቸው። 40  በኋላም ሰዎቹ እንዲበሉ አቀረቡላቸው፤ እነሱ ግን ወጡን ገና እንደቀመሱት “የእውነተኛው አምላክ ሰው ሆይ፣ ድስቱ ውስጥ ገዳይ መርዝ አለ” ብለው ጮኹ። ሊበሉትም አልቻሉም። 41  እሱም “ዱቄት አምጡልኝ” አለ። ዱቄቱንም ድስቱ ውስጥ ከጨመረው በኋላ “ለሰዎቹ አቅርቡላቸው” አለ። በድስቱም ውስጥ ጉዳት የሚያስከትል ምንም ነገር አልተገኘም።+ 42  ከበዓልሻሊሻ+ የመጣ አንድ ሰው ነበር፤ እሱም ለእውነተኛው አምላክ ሰው ከፍሬው በኩራት የተዘጋጁ 20 የገብስ ዳቦዎችና+ አንድ ከረጢት የእሸት ዛላዎች ይዞለት መጣ።+ ከዚያም ኤልሳዕ “ሰዎቹ እንዲበሉ ስጣቸው” አለው። 43  ሆኖም አገልጋዩ “ይህን እንዴት አድርጌ ለ100 ሰው አቀርባለሁ”+ አለው። በዚህ ጊዜ ኤልሳዕ “ሰዎቹ እንዲበሉ ስጣቸው፤ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፦ ‘ይበላሉ፤ ደግሞም ይተርፋቸዋል’”+ አለው። 44  ከዚያም አቀረበላቸው፤ እነሱም በሉ፤ ይሖዋም በተናገረው መሠረት ተረፋቸው።+

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ነፍሷ በውስጧ እጅግ ተመራለች።”
ወይም “በሕያው ነፍስህ።”