ሁለተኛ ነገሥት 9:1-37

  • ኢዩ የእስራኤል ንጉሥ እንዲሆን ተቀባ (1-13)

  • ኢዩ ኢዮራምንና አካዝያስን ገደላቸው (14-29)

  • ኤልዛቤል ተገደለች፤ ሥጋዋን ውሾች በሉት (30-37)

9  ከዚያም ነቢዩ ኤልሳዕ ከነቢያት ልጆች አንዱን ጠርቶ እንዲህ አለው፦ “ልብስህን በወገብህ ታጠቅና ይህን የዘይት ዕቃ ይዘህ ወደ ራሞትጊልያድ+ በፍጥነት ሂድ።  እዚያም ስትደርስ የኒምሺን ልጅ፣ የኢዮሳፍጥን ልጅ ኢዩን+ ፈልገው፤ ከዚያም ገብተህ ከወንድሞቹ መካከል አስነሳውና ወደ ውስጠኛው ክፍል ውሰደው።  የዘይቱንም ዕቃ ወስደህ ዘይቱን በራሱ ላይ አፍስ፤ እንዲህም በለው፦ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “አንተን በእስራኤል ላይ ንጉሥ አድርጌ ቀብቼሃለሁ።”’+ ከዚያም በሩን ከፍተህ በፍጥነት ሽሽ።”  በመሆኑም የነቢዩ አገልጋይ ወደ ራሞትጊልያድ አቀና።  እዚያም ሲደርስ የሠራዊቱ አለቆች ተቀምጠው አገኛቸው። እሱም “አለቃ ሆይ፣ የምነግርህ መልእክት አለኝ” አለ። ኢዩም “ለማናችን ነው?” ሲል ጠየቀው። እሱም “አለቃ ሆይ፣ ለአንተ ነው” አለው።  በመሆኑም ኢዩ ተነስቶ ወደ ቤት ገባ፤ አገልጋዩም ዘይቱን በኢዩ ራስ ላይ በማፍሰስ እንዲህ አለው፦ “የእስራኤል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘አንተን በይሖዋ ሕዝብ፣ በእስራኤል ላይ ንጉሥ አድርጌ ቀብቼሃለሁ።+  አንተም የጌታህን የአክዓብን ቤት ትመታለህ፤ እኔም የአገልጋዮቼን የነቢያትን ደምና በኤልዛቤል እጅ የሞቱትን የይሖዋን አገልጋዮች ሁሉ ደም እበቀላለሁ።+  የአክዓብም ቤት በጠቅላላ ይጠፋል፤ ደግሞም በእስራኤል ውስጥ ያለውን ምስኪኑንም ሆነ ደካማውን ጨምሮ ከአክዓብ ቤት ወንድ የተባለውን ሁሉ* ጠራርጌ አጠፋለሁ።+  የአክዓብንም ቤት እንደ ናባጥ ልጅ እንደ ኢዮርብዓም ቤትና+ እንደ አኪያህ ልጅ እንደ ባኦስ ቤት+ አደርገዋለሁ። 10  ኤልዛቤልን ደግሞ ኢይዝራኤል ውስጥ በሚገኝ የእርሻ ቦታ ውሾች ይበሏታል፤+ የሚቀብራትም አይኖርም።’” ይህን ከተናገረም በኋላ በሩን ከፍቶ ሸሸ።+ 11  ኢዩ ወጥቶ ወደ ጌታው አገልጋዮች ሲሄድ “ሁሉም ነገር ደህና ነው? ይህ እብድ ወደ አንተ የመጣው ለምንድን ነው?” ብለው ጠየቁት። እሱም “መቼም ሰውየውንም ሆነ የሚናገረውን ነገር ታውቁታላችሁ” አላቸው። 12  እነሱ ግን “ይሄ እንኳ ትክክል አይደለም! ይልቅስ እውነቱን ንገረን” አሉት። ከዚያም ኢዩ “እንግዲህ የነገረኝ ይህ ነው፤ ደግሞም እንዲህ ብሏል፦ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “በእስራኤል ላይ ንጉሥ አድርጌ ቀብቼሃለሁ።”’”+ 13  በዚህ ጊዜ እያንዳንዳቸው ቶሎ ብለው ልብሳቸውን በማውለቅ ደረጃዎቹ ላይ አነጠፉለት፤+ ቀንደ መለከትም ነፍተው “ኢዩ ነግሦአል!” አሉ።+ 14  ከዚያም የኒምሺ ልጅ፣ የኢዮሳፍጥ ልጅ ኢዩ+ በኢዮራም ላይ አሴረ። ኢዮራም ከሶርያ ንጉሥ ከሃዛኤል+ የተነሳ ከእስራኤል ሁሉ ጋር ሆኖ ራሞትጊልያድን+ እየጠበቀ ነበር። 15  በኋላም ንጉሥ ኢዮራም ከሶርያ ንጉሥ ከሃዛኤል ጋር በተዋጋበት ጊዜ ሶርያውያን ካደረሱበት ቁስል ለማገገም ወደ ኢይዝራኤል+ ተመለሰ።+ ኢዩም “እንግዲህ ከተስማማችሁ* ወደ ኢይዝራኤል ሄዶ ይህን ወሬ የሚያቀብል ሰው እንዳይኖር ማንም ሰው ከከተማዋ ሾልኮ እንዳይወጣ ጠብቁ” አለ። 16  ከዚያም ኢዩ ሠረገላው ላይ ወጥቶ ወደ ኢይዝራኤል ሄደ፤ ምክንያቱም ኢዮራም ቆስሎ በዚያ ተኝቶ ነበር፤ የይሁዳ ንጉሥ አካዝያስም ኢዮራምን ለመጠየቅ ወደዚያ ወርዶ ነበር። 17  ጠባቂውም በኢይዝራኤል ማማ ላይ ቆሞ ሳለ የኢዩ ሰዎች ግር ብለው ሲመጡ አየ። ወዲያውኑም “ሰዎች ግር ብለው ሲመጡ ይታየኛል” አለ። ኢዮራምም “አንድ ፈረሰኛ ጠርተህ ወደ እነሱ ላክ፤ እሱም ‘የመጣችሁት በሰላም ነው?’ ይበላቸው” አለ። 18  ስለሆነም አንድ ፈረሰኛ ወደ ኢዩ ሄዶ “ንጉሡ ‘የመጣችሁት በሰላም ነው?’ ይላል” አለው። ኢዩ ግን “አንተ ስለ ‘ሰላም’ ምን ይመለከትሃል? ይልቅስ ከኋላዬ ተሰለፍ!” አለው። ጠባቂውም “መልእክተኛው እነሱ ጋ ደርሷል፤ ሆኖም አልተመለሰም” በማለት ተናገረ። 19  በመሆኑም ሁለተኛ ፈረሰኛ ላከ፤ እሱም እነሱ ጋ ሲደርስ “ንጉሡ ‘የመጣችሁት በሰላም ነው?’ ይላል” አለ። ኢዩ ግን “አንተ ስለ ‘ሰላም’ ምን ይመለከትሃል? ይልቅስ ከኋላዬ ተሰለፍ!” አለው። 20  ጠባቂውም “መልእክተኛው እነሱ ጋ ደርሷል፤ ሆኖም አልተመለሰም፤ ሰውየው ሠረገላ አነዳዱ የኒምሺን የልጅ ልጅ* የኢዩን ይመስላል፤ የሚነዳው ልክ እንደ እብድ ነውና” በማለት ተናገረ። 21  ኢዮራምም “ሠረገላዬን አዘጋጁልኝ!” አለ። በመሆኑም የጦር ሠረገላው ተዘጋጀለት፤ የእስራኤል ንጉሥ ኢዮራምና የይሁዳ ንጉሥ አካዝያስም+ በየራሳቸው የጦር ሠረገላ ሆነው ኢዩን ለመገናኘት ወጡ። በኢይዝራኤላዊው በናቡቴ የእርሻ ቦታ+ ላይ ከእሱ ጋር ተገናኙ። 22  ኢዮራምም ኢዩን እንዳየው “ኢዩ፣ የመጣኸው በሰላም ነው?” አለው። እሱ ግን “የእናትህ የኤልዛቤል+ ምንዝርና መተት+ እያለ ምን ሰላም አለ?” አለው። 23  ኢዮራምም ለመሸሽ ወዲያውኑ ሠረገላውን አዙሮ አካዝያስን “አካዝያስ ተታለናል!” አለው። 24  ኢዩም ቀስቱን አስፈንጥሮ ኢዮራምን በትከሻዎቹ መካከል ወጋው፤ ቀስቱም በልቡ በኩል ወጣ፤ ኢዮራምም እዚያው ጦር ሠረገላው ውስጥ ወደቀ። 25  ኢዩም የጦር መኮንኑን ቢድቃርን እንዲህ አለው፦ “አንስተህ በኢይዝራኤላዊው በናቡቴ የእርሻ ቦታ ላይ ጣለው።+ እኔና አንተ በሠረገሎች ሆነን አባቱን አክዓብን እንከተለው በነበረ ጊዜ ይሖዋ ራሱ በእሱ ላይ ይህን ፍርድ እንዳስተላለፈ አስታውስ፦+ 26  ‘“ትናንት የናቡቴን ደምና የልጆቹን ደም እንዳየሁ ሁሉ”+ ይላል ይሖዋ፣ “በዚህ የእርሻ ቦታ ላይ ዋጋህን እከፍልሃለሁ”+ ይላል ይሖዋ።’ በመሆኑም ይሖዋ በተናገረው ቃል መሠረት አንስተህ እርሻው ላይ ጣለው።”+ 27  የይሁዳ ንጉሥ አካዝያስ+ ይህን ሲያይ በአትክልት ቤቱ በኩል ባለው መንገድ ሸሸ። (በኋላም ኢዩ እሱን እያሳደደው “እሱንም ግደሉት!” አለ። እነሱም በይብለአም+ አጠገብ ወደምትገኘው ወደ ጉር ሽቅብ በሚያስወጣው መንገድ ላይ ሠረገላው ውስጥ እንዳለ አቆሰሉት። እሱ ግን ወደ መጊዶ ሸሸ፤ በዚያም ሞተ። 28  ከዚያም አገልጋዮቹ በሠረገላ ጭነው ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት፤ በዳዊት ከተማ+ ከአባቶቹ ጋር በራሱ መቃብር ቀበሩት። 29  አካዝያስ+ በይሁዳ ላይ የነገሠው የአክዓብ ልጅ ኢዮራም በነገሠ በ11ኛው ዓመት ነበር።) 30  ከዚያም ኢዩ ወደ ኢይዝራኤል+ መጣ፤ ኤልዛቤልም+ ይህን ሰማች። በመሆኑም ዓይኖቿን ተኩላና ፀጉሯን አሰማምራ በመስኮት ቁልቁል ትመለከት ጀመር። 31  ኢዩም በቅጥሩ በር በኩል ሲገባ ኤልዛቤል “ጌታውን የገደለው ዚምሪ ምን እንደደረሰበት አታውቅም?” አለችው።+ 32  እሱም ወደ መስኮቱ ቀና ብሎ በመመልከት “ከእኔ ጎን የቆመ ማን ነው? ማን ነው?”+ አለ። ወዲያውኑ ሁለት ወይም ሦስት የሚሆኑ የቤተ መንግሥት ባለሥልጣናት ቁልቁል ተመለከቱት። 33  እሱም “ወደ ታች ወርውሯት!” አላቸው። እነሱም ወረወሯት፤ ደሟም በግድግዳውና በፈረሶቹ ላይ ተረጨ፤ ኢዩም በፈረሶቹ ረጋገጣት። 34  ከዚያም ገብቶ በላ፤ ጠጣም። በኋላም “እባካችሁ ይህችን የተረገመች ሴት አንስታችሁ ቅበሯት። ምንም ቢሆን የንጉሥ ልጅ ናት”+ አላቸው። 35  ሊቀብሯት ሲሄዱ ግን ከራስ ቅሏ፣ ከእግሮቿና ከእጆቿ መዳፍ በስተቀር ምኗንም አላገኙም።+ 36  እነሱም ተመልሰው በነገሩት ጊዜ እንዲህ አላቸው፦ “ይህ እኮ ይሖዋ በአገልጋዩ በቲሽባዊው በኤልያስ አማካኝነት እንዲህ በማለት የተናገረው ቃል ፍጻሜ ነው፦+ ‘በኢይዝራኤል በሚገኘው የእርሻ ቦታ ውሾች የኤልዛቤልን ሥጋ ይበላሉ።+ 37  ሰዎች “ይህች እኮ ኤልዛቤል ናት” እንዳይሉ የኤልዛቤል በድን በኢይዝራኤል የእርሻ ቦታ ላይ እንደ ፍግ ይሆናል።’”

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “ግንብ ላይ የሚሸናውን ሁሉ።” ወንዶችን የሚያናንቅ የዕብራይስጥ አገላለጽ ነው።
ወይም “ነፍሳችሁ ከተስማማች።”
ቃል በቃል “ወንድ ልጅ።”