ሁለተኛ ዜና መዋዕል 34:1-33

  • ኢዮስያስ በይሁዳ ላይ ነገሠ (1, 2)

  • ኢዮስያስ ያካሄደው ተሃድሶ (3-13)

  • የሕጉ መጽሐፍ ተገኘ (14-21)

  • ሕልዳና ጥፋት እንደሚመጣ ትንቢት ተናገረች (22-28)

  • ኢዮስያስ የሕጉን መጽሐፍ ለሕዝቡ አነበበ (29-33)

34  ኢዮስያስ+ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው ስምንት ዓመት ነበር፤ በኢየሩሳሌምም ሆኖ ለ31 ዓመት ገዛ።+  ኢዮስያስም በይሖዋ ፊት ትክክል የሆነውን ነገር አደረገ፤ በአባቱም በዳዊት መንገድ ሄደ፤ ወደ ቀኝም ወደ ግራም ፈቀቅ አላለም።  በነገሠ በ8ኛው ዓመት፣ ገና ልጅ ሳለ የአባቱን የዳዊትን አምላክ መፈለግ ጀመረ፤+ በ12ኛውም ዓመት ይሁዳንና ኢየሩሳሌምን ከፍ ካሉ የማምለኪያ ቦታዎች፣+ ከማምለኪያ ግንዶች፣* ከተቀረጹ ምስሎችና+ ከብረት ከተሠሩ ሐውልቶች* አነጻ።+  በተጨማሪም እሱ በተገኘበት የባአልን መሠዊያዎች አፈራረሱ፤ በላያቸው ላይ የነበሩትንም የዕጣን ማጨሻዎች ሰባበራቸው። ደግሞም የማምለኪያ ግንዶቹን፣* የተቀረጹትን ምስሎችና ከብረት የተሠሩትን ሐውልቶች* ሰባብሮ አደቀቃቸው፤ ከዚያም ለእነሱ ይሠዉ በነበሩት ሰዎች መቃብር ላይ በተነው።+  የካህናቱንም አጥንቶች በመሠዊያዎቻቸው ላይ አቃጠለ።+ በዚህ መንገድ ይሁዳንና ኢየሩሳሌምን አነጻ።  በተጨማሪም ከምናሴ፣ ከኤፍሬምና+ ከስምዖን አንስቶ እስከ ንፍታሌም ባሉት ከተሞች እንዲሁም በዙሪያቸው ባሉ የወደሙ ስፍራዎች ሁሉ፣  መሠዊያዎችን አፈራረሰ፤ የማምለኪያ ግንዶችንና* የተቀረጹትን ምስሎች+ ሰባብሮ አደቀቃቸው፤ በመላው የእስራኤል ምድር የሚገኙትንም የዕጣን ማጨሻዎች ሰባበረ፤+ ከዚያም ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ።  እሱም በነገሠ በ18ኛው ዓመት ምድሪቱንና ቤተ መቅደሱን* ካነጻ በኋላ የአዜልያን ልጅ ሳፋንን፣+ የከተማዋን አለቃ ማአሴያህንና ታሪክ ጸሐፊውን የዮአሃዝን ልጅ ዮአህን የአምላኩን የይሖዋን ቤት እንዲጠግኑ ላካቸው።+  እነሱም ወደ ሊቀ ካህናቱ ወደ ኬልቅያስ መጥተው ወደ አምላክ ቤት የመጣውን ገንዘብ አስረከቡት፤ ገንዘቡም በር ጠባቂዎች ሆነው የሚያገለግሉት ሌዋውያን ከምናሴ፣ ከኤፍሬም፣ ከቀረው የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ+ እንዲሁም ከይሁዳ፣ ከቢንያምና ከኢየሩሳሌም ነዋሪዎች የሰበሰቡት ነበር። 10  ከዚያም በይሖዋ ቤት የሚከናወነውን ሥራ እንዲቆጣጠሩ ለተሾሙት ሠራተኞች ገንዘቡን ሰጧቸው። በይሖዋ ቤት የሚሠሩት ሠራተኞች ደግሞ ቤቱን ለመጠገንና ለማደስ አዋሉት። 11  በመሆኑም ጥርብ ድንጋዮችንና ለማጠናከሪያ የሚያገለግሉ ሳንቃዎችን እንዲሁም የይሁዳ ነገሥታት ትተዋቸው የፈራረሱትን ቤቶች ለመጠገን የሚያስፈልጉ ወራጆችን እንዲገዙ ገንዘቡን ለእጅ ጥበብ ባለሙያዎቹና ለግንበኞቹ ሰጧቸው።+ 12  ሰዎቹም ሥራውን በታማኝነት አከናወኑ።+ በእነሱም ላይ ከሜራራውያን+ ሌዋውያኑ ያሃት እና አብድዩ፣ ከቀአታውያን+ ደግሞ ዘካርያስ እና መሹላም የበላይ ተመልካቾች ሆነው እንዲያገለግሉ ተሹመው ነበር። የሙዚቃ መሣሪያዎችን በመጫወት የተካኑት ሌዋውያንም ሁሉ፣+ 13  በጉልበት ሠራተኞቹ* ላይ ተሹመው ነበር፤ እንዲሁም በሁሉም ዓይነት አገልግሎት ላይ ተመድበው በሚሠሩት ሠራተኞች ላይ የበላይ ተመልካቾች ሆነው ያገለግሉ ነበር፤ ከሌዋውያኑም መካከል አንዳንዶቹ ጸሐፊዎች፣ አለቆችና በር ጠባቂዎች ነበሩ።+ 14  ወደ ይሖዋ ቤት የመጣውን ገንዘብ በሚያወጡበት+ ጊዜ ካህኑ ኬልቅያስ በሙሴ በኩል* የተሰጠውን+ የይሖዋን ሕግ መጽሐፍ+ አገኘ። 15  በመሆኑም ኬልቅያስ ጸሐፊውን ሳፋንን “የሕጉን መጽሐፍ በይሖዋ ቤት ውስጥ አገኘሁት” አለው። ከዚያም ኬልቅያስ መጽሐፉን ለሳፋን ሰጠው። 16  ሳፋንም መጽሐፉን ወደ ንጉሡ ወስዶ እንዲህ አለው፦ “አገልጋዮችህ የተመደበላቸውን ሥራ ሁሉ እያከናወኑ ነው። 17  በይሖዋ ቤት የተገኘውን ገንዘብ አውጥተው ለተሾሙት ሰዎችና ለሠራተኞቹ አስረክበዋል።” 18  በተጨማሪም ጸሐፊው ሳፋን ንጉሡን “ካህኑ ኬልቅያስ የሰጠኝ አንድ መጽሐፍ አለ” አለው።+ ከዚያም ሳፋን መጽሐፉን በንጉሡ ፊት ማንበብ ጀመረ።+ 19  ንጉሡ የሕጉን ቃል ሲሰማ ልብሱን ቀደደ።+ 20  ከዚያም ንጉሡ ኬልቅያስን፣ የሳፋንን ልጅ አኪቃምን፣+ የሚክያስን ልጅ አብዶንን፣ ጸሐፊውን ሳፋንን እና የንጉሡን አገልጋይ አሳያህን እንዲህ ሲል አዘዛቸው፦ 21  “ሄዳችሁ በተገኘው መጽሐፍ ላይ የሰፈረውን ቃል በተመለከተ እኔን እንዲሁም በእስራኤልና በይሁዳ የቀረውን ሕዝብ ወክላችሁ ይሖዋን ጠይቁ፤ አባቶቻችን በዚህ መጽሐፍ የተጻፉትን ነገሮች ሁሉ ስላልፈጸሙና የይሖዋን ቃል ስላልጠበቁ በእኛ ላይ የሚወርደው የይሖዋ ቁጣ ታላቅ ነው።”+ 22  በመሆኑም ኬልቅያስና ንጉሡ የላካቸው ሰዎች ወደ ነቢዪቱ+ ሕልዳና ሄዱ። ሕልዳና የሃርሐስ ልጅ፣ የቲቅዋ ልጅ፣ የአልባሳት ጠባቂው የሻሉም ሚስት ስትሆን ኢየሩሳሌም ውስጥ በሁለተኛው ክፍል ትኖር ነበር፤ እነሱም በዚያ አነጋገሯት።+ 23  እሷም እንዲህ አለቻቸው፦ “የእስራኤል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘ወደ እኔ የላካችሁን ሰው እንዲህ በሉት፦ 24  “ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘በዚህ ቦታና በነዋሪዎቹ ላይ መከራ አመጣለሁ፤+ በይሁዳ ንጉሥ ፊት ባነበቡት መጽሐፍ ላይ የሰፈረውን እርግማን ሁሉ አመጣለሁ።+ 25  እኔን በመተው+ በእጆቻቸው ሥራ ሁሉ ያስቆጡኝ ዘንድ ለሌሎች አማልክት የሚጨስ መሥዋዕት ስለሚያቀርቡ+ በዚህ ቦታ ላይ ቁጣዬ ይፈስሳል፤ ደግሞም አይጠፋም።’”+ 26  ይሖዋን እንድትጠይቁ ለላካችሁ ለይሁዳ ንጉሥ ግን እንዲህ በሉት፦ “የእስራኤል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘የሰማኸውን ቃል በተመለከተ፣+ 27  ስለዚህ ቦታና ስለ ነዋሪዎቹ የተናገረውን ቃል ስትሰማ ልብህ ስለተነካና* በአምላክ ፊት ራስህን ስላዋረድክ እንዲሁም ራስህን በፊቴ ዝቅ ስላደረግክ፣ ልብስህን ስለቀደድክና በፊቴ ስላለቀስክ እኔም ሰምቼሃለሁ ይላል ይሖዋ።+ 28  ወደ አባቶችህ የምሰበስብህ* በዚህ የተነሳ ነው፤ አንተም በሰላም በመቃብርህ ታርፋለህ፤ በዚህ ቦታና በነዋሪዎቹ ላይ የማመጣውን መከራ ሁሉ ዓይኖችህ አያዩም።’”’”+ ከዚያም ሰዎቹ መልሱን ለንጉሡ አመጡለት። 29  ንጉሡም መልእክት ልኮ የይሁዳንና የኢየሩሳሌምን ሽማግሌዎች ሁሉ ጠራ።+ 30  ከዚያ በኋላ ንጉሡ ከይሁዳ ሰዎች፣ ከኢየሩሳሌም ነዋሪዎች፣ ከካህናቱ፣ ከሌዋውያኑ እንዲሁም ትልቅ ትንሽ ሳይባል ከሕዝቡ ሁሉ ጋር ወደ ይሖዋ ቤት ወጣ። እሱም በይሖዋ ቤት የተገኘውን የቃል ኪዳኑን መጽሐፍ ቃል ሁሉ የተሰበሰቡት ሰዎች እየሰሙ አነበበላቸው።+ 31  ንጉሡ ባለበት ስፍራ ቆሞ፣ በዚህ መጽሐፍ ላይ የሰፈሩትን የቃል ኪዳኑን ቃላት በመፈጸም+ በሙሉ ልቡና በሙሉ ነፍሱ*+ ይሖዋን ለመከተል እንዲሁም ትእዛዛቱን፣ ማሳሰቢያዎቹንና ሥርዓቶቹን ለመጠበቅ በይሖዋ ፊት ቃል ኪዳን ገባ።*+ 32  በተጨማሪም በኢየሩሳሌምና በቢንያም ያሉት ሁሉ በቃል ኪዳኑ እንዲስማሙ አደረገ። የኢየሩሳሌምም ነዋሪዎች በአምላክ ይኸውም በአባቶቻቸው አምላክ ቃል ኪዳን መሠረት እርምጃ ወሰዱ።+ 33  ከዚያም ኢዮስያስ ከመላው የእስራኤላውያን ምድር አስጸያፊዎቹን ነገሮች* በሙሉ አስወገደ፤+ እንዲሁም በእስራኤል ያሉ ሁሉ አምላካቸውን ይሖዋን እንዲያገለግሉ አደረገ። በሕይወት ዘመኑ* ሁሉ የአባቶቻቸውን አምላክ ይሖዋን ከመከተል ፈቀቅ አላሉም።

የግርጌ ማስታወሻ

ወይም “ቀልጠው ከተሠሩ ሐውልቶች።”
ወይም “ቀልጠው የተሠሩትን ሐውልቶች።”
ቃል በቃል “ቤቱን።”
ወይም “በተሸካሚዎቹ።”
ቃል በቃል “እጅ።”
ቃል በቃል “ልብህ ስለለሰለሰና።”
ይህ ሞትን የሚያመለክት ቅኔያዊ አነጋገር ነው።
ወይም “ቃል ኪዳኑን አደሰ።”
ወይም “ጣዖታቱን።”
ቃል በቃል “በቀኖቹ።”