ሁለተኛ ዜና መዋዕል 35:1-27

  • ኢዮስያስ ታላቅ የፋሲካ በዓል እንዲከበር ዝግጅት አደረገ (1-19)

  • የግብፁ ንጉሥ ኒካዑ ኢዮስያስን ገደለው (20-27)

35  ኢዮስያስ በኢየሩሳሌም ለይሖዋ ፋሲካ አደረገ፤+ በመጀመሪያው ወር በ14ኛው ቀን+ የፋሲካን መሥዋዕት አረዱ።+  ካህናቱን በየሥራቸው ላይ መደባቸው፤ የይሖዋንም ቤት አገልግሎት እንዲያከናውኑ አበረታታቸው።+  ከዚያም የመላው እስራኤል አስተማሪዎች+ የሆኑትንና ለይሖዋ የተቀደሱትን ሌዋውያን እንዲህ አላቸው፦ “ቅዱሱን ታቦት የእስራኤል ንጉሥ የዳዊት ልጅ ሰለሞን በሠራው ቤት ውስጥ አስቀምጡት፤+ ከዚህ በኋላ ታቦቱን በትከሻችሁ መሸከም አያስፈልጋችሁም።+ አሁን አምላካችሁን ይሖዋንና ሕዝቡን እስራኤልን አገልግሉ።  የእስራኤል ንጉሥ ዳዊትና+ ልጁ ሰለሞን+ በጻፉት ትእዛዝ መሠረት በየአባቶቻችሁ ቤት እንደየምድባችሁ ራሳችሁን አዘጋጁ።  ወንድሞቻችሁ የሆኑትን የቀሩትን ሰዎች* ለማገልገል በየአባቶች ቤት ምድብ በተቀደሰው ስፍራ ቁሙ፤ እያንዳንዱም የሌዋውያን ቡድን ከሕዝቡ መካከል የሚደርሰውን የአባቶች ቤት ምድብ ያገልግል።  የፋሲካውን መሥዋዕት እረዱ፤+ ራሳችሁንም ቀድሱ፤ ይሖዋ በሙሴ በኩል የሰጠውን ትእዛዝ መፈጸም እንድትችሉ ለወንድሞቻችሁ አስፈላጊውን ዝግጅት አድርጉ።”  ኢዮስያስም ለሕዝቡ ይኸውም በዚያ ለተገኙት ሁሉ ለፋሲካ መሥዋዕት እንዲሆኑ ከመንጋው መካከል በድምሩ 30,000 ተባዕት የበግና የፍየል ጠቦቶች እንዲሁም 3,000 ከብቶች ሰጠ። እነዚህ የተሰጡት ከንጉሡ ሀብት ላይ ነበር።+  መኳንንቱም ለሕዝቡ፣ ለካህናቱና ለሌዋውያኑ በፈቃደኝነት የሚቀርብ መባ ሰጡ። የእውነተኛው አምላክ ቤት መሪዎች የሆኑት ኬልቅያስ፣+ ዘካርያስና የሂኤል ለፋሲካ መሥዋዕት የሚሆኑ 2,600 በጎችና ፍየሎች እንዲሁም 300 ከብቶች ለካህናቱ ሰጡ።  ኮናንያ፣ ወንድሞቹ ሸማያህ እና ናትናኤል እንዲሁም የሌዋውያኑ አለቆች ሃሻብያህ፣ የኢዔል እና ዮዛባድ ለፋሲካ መሥዋዕት የሚሆኑ 5,000 በጎችና ፍየሎች እንዲሁም 500 ከብቶች ለሌዋውያኑ ሰጡ። 10  የአገልግሎቱ ዝግጅት ከተጠናቀቀ በኋላ ንጉሡ ባዘዘው መሠረት ካህናቱ በየቦታቸው፣ ሌዋውያኑም በየምድባቸው+ ቆሙ። 11  የፋሲካውንም መሥዋዕት አረዱ፤+ ሌዋውያኑ ቆዳውን ሲገፉ+ ካህናቱ ደግሞ ከእነሱ የተቀበሉትን ደም መሠዊያው ላይ ረጩ።+ 12  ከዚያም በየአባቶች ቤት ለተመደቡት ለቀሩት ሰዎች ለማከፋፈል የሚቃጠለውን መባ አዘጋጁ፤ ይህም የሆነው በሙሴ መጽሐፍ ላይ በተጻፈው መሠረት መባው ለይሖዋ እንዲቀርብ ነው፤ ከብቶቹንም በዚሁ መንገድ አዘጋጁ። 13  በልማዱም መሠረት የፋሲካን መባ በእሳት አበሰሉ፤*+ የተቀደሱትንም መባዎች በድስት፣ በሰታቴና በመጥበሻ አብስለው ወዲያውኑ ለቀሩት ሰዎች ሁሉ አቀረቡ። 14  ከዚያም ለራሳቸውና ለካህናቱ አዘጋጁ፤ ምክንያቱም የአሮን ዘሮች የሆኑት ካህናቱ እስኪመሽ ድረስ፣ የሚቃጠሉትን መሥዋዕቶችና ስቡን ያቀርቡ ነበር፤ በመሆኑም ሌዋውያኑ ለራሳቸውና የአሮን ዘሮች ለሆኑት ለካህናቱ አዘጋጁ። 15  ዳዊት፣+ አሳፍ፣+ ሄማንና የንጉሡ ባለ ራእይ የሆነው የዱቱን+ በሰጡት ትእዛዝ መሠረት የአሳፍ+ ልጆች የሆኑት ዘማሪዎቹ በየቦታቸው ላይ ነበሩ፤ በር ጠባቂዎቹም በየበሩ ላይ ነበሩ።+ ወንድሞቻቸው የሆኑት ሌዋውያን አዘጋጅተውላቸው ስለነበር ሥራቸውን ትተው መሄድ አላስፈለጋቸውም። 16  በመሆኑም ንጉሥ ኢዮስያስ ባዘዘው መሠረት+ ፋሲካን ለማክበርና+ በይሖዋ መሠዊያ ላይ የሚቃጠለውን መባ ለማቅረብ፣ ለይሖዋ አገልግሎት የሚያስፈልገው ነገር ሁሉ በዚያን ቀን ተዘጋጅቶ ነበር። 17  በስፍራው የተገኙት እስራኤላውያን በዚያ ጊዜ ፋሲካን አከበሩ፤ የቂጣንም በዓል ለሰባት ቀን አከበሩ።+ 18  ከነቢዩ ሳሙኤል ዘመን ወዲህ እንደዚህ ያለ የፋሲካ በዓል በእስራኤል ተከብሮ አያውቅም፤ ኢዮስያስ፣ ካህናቱ፣ ሌዋውያኑ፣ በዚያ የተገኙት የይሁዳና የእስራኤል ሰዎች ሁሉ እንዲሁም የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ያከበሩት ዓይነት ፋሲካ ያከበረ አንድም የእስራኤል ንጉሥ የለም።+ 19  ይህ ፋሲካ የተከበረው ኢዮስያስ በነገሠ በ18ኛው ዓመት ነበር። 20  ከዚህ ሁሉ በኋላ ኢዮስያስ ቤተ መቅደሱን* አዘጋጅቶ ባጠናቀቀ ጊዜ የግብፁ ንጉሥ ኒካዑ+ በኤፍራጥስ አጠገብ ባለው በካርከሚሽ ለመዋጋት መጣ። በዚህ ጊዜ ኢዮስያስ ሊገጥመው ወጣ።+ 21  ኒካዑም እንዲህ ሲል መልእክተኞችን ላከበት፦ “የይሁዳ ንጉሥ ሆይ፣ እኔን ልትወጋ የመጣኸው ለምንድን ነው? አሁን የመጣሁት ከሌላ ብሔር ጋር ልዋጋ እንጂ አንተን ልወጋ አይደለም፤ አምላክም እንድፈጥን አዞኛል። ከእኔ ጋር የሆነውን አምላክ መቃወም ቢቀርብህ ይሻላል፤ አለዚያ ያጠፋሃል።” 22  ኢዮስያስ ግን ለመመለስ ፈቃደኛ አልሆነም፤ ይልቁንም ማንነቱ እንዳይታወቅ ራሱን ለውጦ+ ከእሱ ጋር ለመዋጋት ወጣ፤ በኒካዑ በኩል የተነገረውን የአምላክ ቃል አልሰማም። በመሆኑም ለመዋጋት ወደ መጊዶ+ ሜዳ መጣ። 23  ቀስተኞችም ንጉሥ ኢዮስያስን ወጉት፤ ንጉሡም አገልጋዮቹን “ክፉኛ ስለቆሰልኩ ከዚህ አውጡኝ” አላቸው። 24  በመሆኑም አገልጋዮቹ ከሠረገላው አውርደው በሁለተኛው የጦር ሠረገላው ላይ ካስቀመጡት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት። እሱም በዚህ ሁኔታ ሞተ፤ በአባቶቹም መቃብር ተቀበረ፤+ የይሁዳና የኢየሩሳሌም ሰዎች ሁሉ ለኢዮስያስ አለቀሱ። 25  ኤርምያስም+ ለኢዮስያስ የሐዘን እንጉርጉሮ ተቀኘ፤ ወንዶችና ሴቶች ዘማሪዎችም+ ሁሉ እስከ ዛሬ ድረስ በሙሿቸው* ላይ ስለ ኢዮስያስ ይዘምራሉ፤ ደግሞም በእስራኤል እንዲዘመርና ሌሎች ሙሾዎች በተጻፉበት መጽሐፍ ላይ እንዲሰፍር ተወሰነ። 26  የቀረው የኢዮስያስ ታሪክና በይሖዋ ሕግ ላይ በተጻፈው መሠረት ያከናወናቸው ታማኝ ፍቅር የተንጸባረቀባቸው ተግባራት 27  እንዲሁም ከመጀመሪያ አንስቶ እስከ መጨረሻ ድረስ ያደረጋቸው ነገሮች በእስራኤልና በይሁዳ ነገሥታት መጽሐፍ ተጽፈዋል።+

የግርጌ ማስታወሻ

ቃል በቃል “የሕዝቡን ወንዶች ልጆች።”
“ጠበሱ” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ቃል በቃል “ቤቱን።”
ወይም “በሐዘን እንጉርጉሯቸው።”